ባለሀብቶችን በመሰለል፣ በማገት እና በማስፈራራት 8 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በጠየቁ እና በተቀበሉ አራት የመከላከያ ሚኒስቴር አባላት እና ግብረ-አበሮቻቸው ላይ ሥልጣንን አላግባብ በመገልገል ከባድ የሙስና ወንጀል ስር ክስ መመሥረቱን ፍትሕ ሚኒስቴር አስታወቀ።
ክሱ የተመሠረተው የመከላከያ መኪና በመያዝ “ከጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ሀብት ማስመለስ የመጣን ዐቃቤ ሕጎች ነን፤ ሕገ-ወጥ ዘይት፣ ስኳር እና የጦር መሣርያ ስለምትሸጡ በወንጀል ትፈለጋላችሁ” በማለት 8 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በጠየቁ የመከላከያ ሚኒስቴር አባላት እና ግብረ-አበሮቻቸው ላይ ነው።
የተለያዩ የምርምራ ሂዶትችን ከፖሊስ ጋር ሲያከናውን ቆይቶ በግለሰቦች ላይ ክሱን የመሠረተው ደግሞ በጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ የሙስና ወንጀል ጉዳዮች ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት ጄኔራል መሆኑ ተገልጿል።
ወንጀሉን ፈጽመዋል በሚል ክስ የተመሠረተባቸው በመከላከያ ሚኒስቴር በ93ኛ እና 94ኛ እግረኛ ክፍለ ጦር አባል የሆኑት 1ኛ) መቶ አለቃ ሀጂ ቱሉ߹ 2ኛ) ኦፊሰር መንግሥቱ በቀለ߹ 3ኛ) ሻምበል ካህሊ መላክ߹ 4ኛ) ሻለቃ ዱጉማ ዲምሳ እና በተለያዩ የንግድ ሥራዎች ውስጥ ተሰማርተው የሚገኙት ግብረ-አበሮቻቸው ከ5ኛ-8ኛ ስማቸው በክሱ የተጠቀሰው ተከሳሾች ሹምበዛ ፍቃዱ፣ አዲስ ዓለሙ፣ ተስፋዬ ለሚ እና አሸናፊ ወልደ ሰማያት መሆናቸውን ከፍትሕ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
ችሎቱ በቁጥጥር ስር ያልዋሉትን 7ኛ እና 8ኛ ተከሳሽን ፖሊስ አፈላልጎ አንዲያቀርብ ትዕዛዝ የሰጠ ሲሆን ተከሳሾች በተመሰረተባቸው ክስ ላይ የመጀመርያ የክስ መቃወሚያ እና ባልተያዙ ተከሳሾች ላይ የፖሊስን ምላሽ ለመጠባበቅ ለግንቦት 29/2014 ዓ.ም ቀጠሮ ተሰጥቷል።
ግንቦት 22/2014 (ዋልታ)