በጎንደር እጃቸው የያዙት ቦምብ ይሰራል አይሰራም በሚል ሲከራከሩ ፈንድቶ አራት ሰዎች ሕይወታቸው አለፈ

November 6, 2018

በሰሜን ጎንደር ደባርቅ ወረዳ አደባባይ ፅዮን ቀበሌ ኤፍ ዋን የተባለ ቦንብ በግለሰብ ቤት ሲነካኩ በመፈንዳቱ 4 ሰዎች የሞት አደጋ 2 ሰዎች ደግሞ ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው የደባርቅ ወረዳ ፖሊስ ፅ/ቤት ገለፀ፡፡

በአደጋው የእግርና የእጅ ጉዳት የደረሰባቸው አቶ አወቀ ሲሳይ ለደባርቅ ወረዳ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት እንደገለጹት አደጋው ከደረሰበት ቤት ድግስ ለመብላት እንደተሰባሰቡና በጨዋታ መሃል የቤቱ ባለቤት ቦንቡን በማውጣት ይሰራል አይሰራም በሚል ክርክር ሲነካኩት እንደፈነዳ ገልፀዋል፡፡ በአደጋው በቤቱ ከነበሩት 7 ሰዎች 4ቱ ሰዎች ወዲያውኑ እንደሞቱ 2ቱ ደግሞ ከባድ ጉዳት እንደደረሰ ባቸው ተናግረዋል፡፡
የወረዳው ፖሊስ ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት ዋና ኢነስፔክተር ቢሆነኝ እልፍ አሰገድ አደጋው የደረሰው ህገ ወጥ ኤፍ ዋን ቦንብ በግለሰብ ቤት አስቀምጠው በማያውቁት ሲነካኩት ፈንድቶ ጉዳት እንደደረሰ ገልፀዋል፡፡ ዋና ኢንስፔክተሩ ቦንቡ ያልተመዘገበና ህገ ወጥ የቡድን መሳሪያ መሆኑን ገልፀው ህብረተሰቡ ከህገ ወጥ መሳሪያ ዝውውር መቆጠብ እንዳለበትና ያረጁ መሳሪያዎችን ወድቀው ሲያገኙ ለፀጥታ አካል መናገር እንደሚገባ እንዲሁም ህገ ወጥ የመሳሪያ አዘዋዋሪዎችንም ለህግ አካል በመጠቆም የዜግነት ግዴታቸውን መወጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡
የጽ/ቤቱ ሁለ ገብ ወንጀል መርማሪ ኦፊሰር የሆኑት ዋና ሳጅን ሊቁ ችሎት ደግሞ አደጋው የተከሰተው በህገ ወጥ መሳሪያ መሆኑን ተናግረው ህብረተሰቡ የዚህ አይነት አደጋ እንዳይደርስበት ስለ መሳሪያ አያያዝ ግንዛቤ በመፍጠር ና ህገ ወጥ መሳሪያም ዝውውር እንዳያደርጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት እየሰጠን ነው ብለዋል፡፡ የህገ ወጥ የመሳሪያ ዝውውር ጉዳቱ ለአዘዋዋሪው ስለሆነ ከዚህ ተግባር መታቀብ እነደሚገባም ጨምረው ገልፀዋል ሲል የኮምዩኒከሽን ጽህፈት ቤቱ ይፋ አድርጓል::

https://www.youtube.com/watch?v=0OBDIk-J-Do&t=71s

Previous Story

ፓርላማው አዲስ ታሪክ ሰራ

Next Story

ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አምባሳደሮችን ሾመ

Go toTop