በአዲስ አበባ በሚገኘው ማጂክ ካርፔት ትምህርት ቤት ውስጥ በትላንትናው እለት 15 ተማሪዎች ራሳቸውን ስተው ወደቁ፡፡
ራሳቸውን የሳቱት የጓደኛቸውን ሞት በድንገት በመስማታቸው ምክንያት እንደነበር ትምህርት ቤቱ ተናግሯል።
በትምህርት ቤቱ የ10ኛ ክፍል ተማሪ የነበረ ወጣት ከትናንትና በስቲያ ባልታወቀ ሁኔታ በክፍል ውስጥ እንዳለ በጓደኛው ትከሻ ላይ መዝለፍለፉንለአዲስ ዘመን ጋዜጣ የገለጹት ርዕሰ መምህሩ አቶ ወንድሙ እሸቱ አቶ ወንድሙ፤ በወቅቱም ከትምህርት ቤቱ አጠገብ በሚገኝ ጤና ጣቢያ ተወስዶ ህክምና ቢደረግለትም የልብ ምቱ በፍጥነት በመቆሙ ህይወቱ ማለፉን ተናግረዋል። የአሟሟት ሁኔታውን ለመረዳት እንዲቻልም የአስክሬን ምርመራ ተደርጎ ውጤቱ እየተጠበቀ መሆኑን አስረድተዋል።
እንደ አቶ ወንድሙ ገለጻ፤ በትምህርት ቤቱ የተገኙ ተማሪዎች ትላንትና የጓደኛቸውን ህልፈት ሲረዱ በግቢው ውስጥ ኀዘናቸውን በመግለጽ ላይ እያሉ የተደናገጡ ከሰባተኛ እስከ አስረኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች እራሳቸውን ስተው ወድቀዋል። በወቅቱ ግን በመገናኛ ብዙኃን ተማሪዎች እና መምህራን ጸብ ፈጥረው ጉዳት መድረሱን የሚገልጽ የተሳሳተ መረጃ በመተላለፉ ወላጆች ተደናግጠው ትምህርት ቤቱን አጨናንቀውት ነበር።
በትምህርት ቤቱ አጠገብ የሚገኘው የወረዳ ስምንት ጨፌ ጤና ጣቢያ ጤና መኮንን ሒሩት ተክለጻዲቅ እንደገለጹት፤ በተወሰነ መልኩ እራሳቸውን የሳቱ (ሰሚ ኮንሺየስ) ሆነው ወደ ጤና ጣቢያው የመጡ 15 የሚደርሱ ተማሪዎች ህክምና አግኝተው ተመልሰዋል። ‹‹በተማሪው ሞት ምክንያት እንግዳ የሆነ ነገር የተፈጠረባቸው በመሆኑ አሳሳቢ የህክምና ችግር አልታየባቸውም። በወቅቱም ከአቅም በላይ የሆነ ችግር ቢያጋጥም በሚል ሁለት አምቡላንሶች ዝግጁ ሆነው ነበር።›› ብለዋል የጤና መኮንኗ፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=nwAe0H54xdQ