የቀድሞው የአማራ ክልል ልዩ ኃይል አዛዥ ብርጋዴየር ጀኔራል ተፋራ ማሞ ማምሻውን ከእስር መፈታታቸውን ጠበቃቸውና ባለቤታቸው ለዶቼቬለ አረጋገጡ፡፡ ብርጋድየር ጀነራል ተፈራ ከእስር የተፈቱት ዛሬ ያስቻለው የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በ30ሺህ ብር ዋስ እንዲለቀቁ ዛሬ ከሰዓት በኋላ ውሳኔ ከሰጠ በኋላ ነው፡፡
በሽብር ተጠርጥረው ጉዳያቸው በባሕር ዳር አማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሲታይ በቆየው ክርክር ላይ አቃቤ ህግ ትናንት ግለሰቡ በሽብርና በሌሎች ተደራራቢ ወንጀሎች ስለተጠረጠሩ፣ የፍርድ ውሳኔው ከፍተኛ ሊሆን ይችላል ብለው ስለሚያስቡና ሊሰወሩ ወይም ሊጠፉ ስለሚችሉ ግለሰቡ በዋስ ከእስር እንዳይፈቱ በሚል ተሟግቷል፡፡
የተጠርጣሪ ጠበቆች በበኩላቸው የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የማያስከለክል በመሆኑ ደንበኛቸው የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ተከራክረው ነበር፡፡
ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ የተሰየመው የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የግራቀኙን ክርክር ተመልክቶ የተጠረጠሩበት ጉዳይ ዋስትና የማያስከለክል ነው በማለት ዋስትናውን ፈቅዷል፡፡
የጀኔራል ተፈራ ማሞ ባለቤት ወ/ሮ መነን ኃይሌና የተጠርጣሪ ጠበቃ ሸጋው አለበል ጀኔራሉ ከሰዓታት በፊት ከባህር ዳር ማረሚያ ቤት መለቀቃቸውን ለዶይቼ ቬሌ አረጋግጠዋል ሲል አለምነው መኮንን ከባህርዳር ዘግቧል።