የጠቅላይ ምኒስትር አብደላ ሐምዶክ አስተዳደር ከሥልጣን እንዲለቅ ጥሪ

October 17, 2021

 

የሱዳን ጦርን የሚደግፉ በሺሕዎች የሚቆጠሩ የመንግሥት ተቃዋሚዎች ዛሬ ቅዳሜ በኻርቱም አደባባይ ወጡ። በዋና ከተማዋ በሚገኘው ፕሬዝደንታዊ ጽህፈት ቤት ደጃፍ የተሰበሰቡ ተቃዋሚዎች “የረሐብ መንግሥት” ያሉት የጠቅላይ ምኒስትር አብደላ ሐምዶክ አስተዳደር ከሥልጣን እንዲለቅ ጥሪ ማቅረባቸውን ሬውተርስ ዘግቧል። የተቃውሞ ሰልፉ የቀድሞው የሱዳን መሪ ኦማር አል በሺርን ከሥልጣን ለማውረድ ያመጹ ቡድኖችን ጨምሮ ለጦሩ በሚወግኑ የነፃነት እና የለውጥ ኃይሎች ስብስብ አንድ አንጃ የተጠራ ነበር።

“ወታደራዊ መንግሥት ያስፈልገናል። አሁን ያለው መንግሥት ፍትኅ እና እኩልነት ሊያመጣልን አልቻለም” ሲሉ በተቃውሞ ሰልፉ የተሳተፉት የ50 አመቱ አባውድ አሕመድ ተናግረዋል። ተቺዎች ሰልፉ በጦሩ እና በጸጥታ ኃይሎች ግፊት የተደረገ እና የቀድሞው መንግሥት ናፋቂዎች የተካተቱበት ነው ሲሉ ይወነጅላሉ።
ተቃዋሚዎቹ መንግሥት እንዲበተን የሚጠይቁ መፈክሮች ይዘው የታዩ ሲሆን “አንድ ጦር፤ አንድ ሕዝብ” እንዲሁም “ጦሩ ዳቦ ያመጣልናል” ሲሉ መደመጣቸውን የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።
ኢናም መሐመድ የተባሉ የኻርቱም ነዋሪ የቤት እመቤት “ሰላማዊ ተቃውሞ ለማሰማት ነው የወጣነው። ወታደራዊ መንግሥት እንፈልጋለን” በማለት ከአባውድ አሕመድ የተስማማ አስተያየት ሰጥተዋል።
ከተቃውሞው በፊት ማንነታቸው ያልተለየ ታጣቂ ቡድኖች በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ዙሪያ ለጸጥታ ጥበቃ የተዘጋጁ ማገጃዎችን ማንሳታቸውን እና ፖሊስ እና የጸጥታ ኃይሎች ወደ ሥራ እንዳይሔዱ መከልከላቸውን የኻርቱም ግዛት አስተዳዳሪ አይማን ኻሊድ ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
ትናንት አርብ የሱዳኑ ጠቅላይ ምኒስትር አብደላ ሐምዶክ አገራቸው ወደ ሲቪል አስተዳደር የምታደርገው ሽግግር “የከፋ ቀውስ” እንደገጠመው አስጠንቅቀው ነበር።
DW

Leave a Reply

Your email address will not be published.

245328159 2112541888897148 8138488649708454859 n
Previous Story

በሰሜን ሸዋ ዞን ማጀቴ አርሶአደሮች ማሳ ላይ በተፈጸመው ድንገተኛ ጥቃት ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያለው እህል ወድሟል

245485628 2977659155726685 7784293124007292944 n
Next Story

በኢትዮጵያ ፀሐይ ያጠላው ጥቁር ደመና ቹቹ አለባቸው (ከፍትሕ መጽሔት)

Go toTop