ሁለቱን ግለሰቦች ለጨፌ ኦሮሚያ ምክር ቤት ለሹመት ያቀረቡት፤ የኦሮሚያ ክልልን ለቀጣዮቹ አምስት ዓመታት እንዲመሩ ዛሬ በድጋሚ የተመረጡት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ናቸው። በምክር ቤቱ ፊት ቃለ መሃላ የፈጸሙት አቶ ሽመልስ፤ 32 አባላት ያሉበትን ካቢኔያቸውን ለጨፌ ኦሮሚያ በማቅረብ አጸድቀዋል።
በርካታ አዳዲስ ፊቶችን ወደፊት ያመጣውን የዛሬውን የካቢኔ አባላት ሹመት፤ 12 የምክር ቤት አባላት ተቃውመታል። አስራ ሶስት የጨፌ ኦሮሚያ አባላት በሹመቱ ላይ ድምጽ ከመስጠት ታቅበዋል።
የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው የተሾሙት አቶ አወሉ፤ ወደዚህ ኃላፊነት ከመምጣታቸው አስቀድሞ ላለፈው አንድ ዓመት የመለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚን ሲመሩ ቆይተዋል። የመንግስት ከፍተኛ አመራሮች ማሰልጠኛ የሆነው ይህ ተቋም፤ ስያሜውን ወደ አፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ የቀየረው ባለፈው ሰኔ ወር ነበር።
በአዲሱ የኦሮሚያ ክልል ካቢኔ አምስት ኃላፊዎች በምክትል ፕሬዝዳንት ማዕረግ ሹመት አግኝተዋል። በሹመቱ ከተካተቱት ውስጥ ቀደም ሲል በተመሳሳይ ማዕረግ የሰሩት ዶ/ር ግርማ አመንቴ እና አቶ አዲሱ አረጋ ይገኙበታል። ዶ/ር ግርማ የክልሉ ሀብት እና ንብረት ክላስተር አስተባባሪ በመሆን ሲሾሙ፤ አቶ አዲሱ ደግሞ የከተማ ልማት ክላስተር አስተባባሪ ሆነዋል።
በዛሬው የካቢኔ ሹመት፤ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባል የሆኑት አቶ አራርሶ ቢቂላ የቢሮ ኃላፊነት ስልጣን ማግኘታቸው ይፋ ተደርጓል። አቶ አራርሶ የክልሉን ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ በኃላፊነት እንዲመሩ ተሹመዋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)