የሕሊና እስረኞቹን አንዷለም አራጌን እና እስክንድር ነጋን ጨምሮ 746 እስረኞች ሊፈቱ መሆኑ ተዘገበ

February 8, 2018

መንግስታዊው ራድዮ ፋና እንደዘገበው  በፌደራል ደረጃ በተለይም ሽብር፣ በሁከትና ብጥብጥ፣ በሀይማኖት አክራሪነት በሚሉ የማፈኛ ወንጀሎች ተፈርዶባቸው በማረሚያ ቤት የሚገኙ 417 ታራሚዎች በይቅርታ እንዲለቀቁ ተወሰነ።

ጠቅላይ አቃቤ ህግ ገለጸልኝ ያለው ፋና ከታራሚዎቹ መካከል 298 በፌደራል ማረሚያ ቤት የሚገኙ እና 119 በአማራ ክልል ማረሚያ ቤቶች የሚገኙ ናቸው በይቅርታ እንዲለቀቁ የተወሰነው። የታራሚዎቹ ዝርዝር በይቅርታ ቦርድ ለሀገሪቱ ርእሰ ብሔር ቀርቦ ከፀደቀ እና ተገቢውን የተሃድሶ ስልጠና ከወሰዱ በኋላ ወደ ህብረተሰቡ እንደሚቀላቀሉም ነው የተገለፀው።

እንዲለቀቁ ከተወሰነላቸው መካከልም እስክንድር ነጋና አንዱዓለም አራጌ ይገኙበታል።

በተመሳሳይም ራድዮው እንደዘገበው ጉዳያቸው በህግ በመታየት ላይ የነበሩ 329 ተጠርጣሪዎች ክሳቸው እንዲቋረጥ ተወስኗል። በዚሁ መሰረት 278 በፌደራል፣ 18 በአማራ ክልል እና 33 በትግራይ ክልል የሚገኙ ተጠርጣሪዎች ክሳቸው ተቋርጦ የተሃድሶ ስልጠና ከወሰዱ በኋላ እንዲለቀቁ ተወስኗል።

በይቅርታ ፈታኋቸው ብሎ በየሚዲያው ስማቸውን ካስነገረው መካከል የተወሰኑት አለመፈታታቸውን ዘ-ሐበሻ ከዚህ ቀደም መዘገቧ አይዘነጋም::

ይህ ዜና ከተሰማ በኋላ ኮ/ል አለበል አማረ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል::

የተገኘው ድል የህዝብ ነው!
እነ አንዷለም አራጌና እስክንድር ነጋና ጨምሮ በርከት ያለ የህሊና እስረኞች ከእስር ለመፍታት መወሰኑን መስማት ለቤተሰቦቻቸውና ለአድናቂወቻቸው ደስታችን ከፍ ያለ ነው። እርግጥ ከወያኔ የማይታመን ተለዋዋጭ ባሃሪና / ወያኔን ማመን ቀብሮ ነው/ አንጻር ሰወቹ ከየማጎሪያው ወጥተው ቤተሰቦቻቸው ዘንድ ሳይገናኑ ማመን ከባድ ነው።
ቢሆንም እንዲህ አይነት ውሳኔ ከራሱ ከወያኔ መንደር መስማት አይከፋም፣ ይህ ውሳኔ ግን ከወያኔ ርህራሄና ቅን ፍላጎት የመጣ ሳይሆን ህዝቡ ያለማቋረጥ በተለይም ላለፉት ሶሶት አመታት ያለማቋረጥ ባስመዘገበው ድል ነው። አሁንም የተገኘውን ድል በማቀብ፣በተገነችው ትንሿ ድል ሳይዘናጋ፣ ህዝቡ ለበለጠ ነጻነትና ስር ነቀል የስርዓት ለውጥ ለማምጣት የሚያካሂደውን ተጋድሎ አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ይመከራል። ዋናው ነገርም ሰወችን ከመፍታት በተጨመሪ ለእስር የበቁበትን የነጻነት አስተሳሰብን አብሮ መፍታትም ያስፈልጋል።
ከነ አንዷለም አራጌና እስክንድር ነጋ በተጨማሪም ላለፉት አስር ዐመታት ግፍ ሲፈጸምባቸው የቆዩት እማዋይሽ አለሙ፣ ጀኔራል ተፈራ ማሞ፣ ጀኔራል አሳምነው

ጽጌ፣ ኮል ደምሰው አንተነህ፣ ሻለቃ አለሙ ጌትነት ፣ ሻለቃ መኮነን ወርቁና ሌሎችንም እንጠብቃለን!!

Previous Story

ሲግኒቸር ተዘጋ

Next Story

የቦንጋ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች ያስነሱዋቸው የመብት ጥያቄዎችን ተከትሎ የተነሳውን አመፅና ብጥብጥ በማስመልከት ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝብ ሕብረት የተሰጠ ማሳሰቢያ

Go toTop