ወቅቱ አማራ በርካታ ፈተናዎች ያሉበት በመሆኑ ፈተናዎቹን ለመሻገር ተደራጅቶ መንቀሳቀስ ተገቢ መሆኑን ብርጋዴር ጄነራል አሳምነው ጽጌ
ተናገሩ፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=ZdkEBlHGPDA&t=1s
ይህን የተናገሩት በዛሬው እለት በደሴ ከተማ የአማራ ወጣቶች ማህበር በወሎ በተለመሰረተበት ወቅት ነው፡፡ ጄኔራሉ በንግግራቸው ‹‹የሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ መልካም ነገሮችን ይዞ እንደመጣው ሁሉ ጥሩ ያልሆኑ ነገሮችም አሉ፤ በመሆኑም መልካሙን ለማጎልበት እና ችግር ያለበትን ለማስተካከል የአማራ ወጣቶች ሚና የጎላ ነው›› ብለዋል፡፡ የአማራ ክልል የፀጥታ ቢሮ ሀላፊ የሆኑት ጄኔራሉ በዚሁ ንግግራቸው የተደራጀ ሕዝብ ለአካባቢው ልማት፣ ሰላምና ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ስላለው በአማራው መካከል በፍፁም መከፋፈል መኖር እንደሌለበትም መክረዋል፡፡
‹‹ከአሁን በፊት በአማራ ክልል ውስጥ ወንድም ወንድሙን እየገደለ፣ እየዘረፈ እና እያሰቃየ እንዲኖር ሲደረግ ኖሯል፤ አሁን አንድ ሆነን መቆም መቻል አለብን›› ብለዋል ብርጋዴር ጀነራል አሳምነው ጽጌ፡፡
የአማራ ወጣቶች ማኅበር በወሎ ሲመሠረት ከደቡብና ከሰሜን ወሎ ዞኖች ሁሉም ወረዳዎች እና ከኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር ተወካዮች ተገኝተዋል፡፡ ወጣቶቹ በአማራነት እና በሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መክረዋል ተብሏል፡፡