የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አሸናፊ እጅጉን አሰናበተ፤ ም/ል ፕሬዚዳንቱ ራሳቸውን አሰናበቱ

June 24, 2013

አሸናፊ እጅጉ(ዘ-ሐበሻ) የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ሰሞኑን ብሔራዊ ቡድኑ ላይ የተከሰተውን ችግር አስመልክቶ ውይይት ለማድረግ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ በመጥራት እየተወያየ ሲሆን በብራዚል አስተናጋጅነት በአውሮፓውያኑ 2014 ለሚካሄደው የዓለም ዋንጫ ላይ ለመሳተፍ የማጣሪያ ጨዋታዎችን በማድረግ ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ሁለት ቢጫ የተሠጠው ተጫዋች ማሰለፉን ተከትሎ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ፌዴሬሽኖች ማህበር ( ፊፋ ) ማጣራት እያደረገ መሆኑን ማሳወቁ ይታወሳል። ይህን ተከትሎ ኢትዮጵያ 3ለ0 እንደተሸነፈች እና 3 ነጥብ እንደሚቀንስባት ከተገለጸ በኋላ እየተደረገ ባለው የጊዮን ሆቴሉ ጉባኤ አቶ አሸናፊ እጅጉን ከጸሐፊነት ከኃላፊነታቸው ማንሳቱ የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ጠቁመዋል።
ፌዴሬሽኑም ዋልያዎቹ ሰኔ አንድ ቀን 2005 ዓ.ም ሎባትሴ ላይ ከቦትስዋና አቻው ጋር ባደረጉት ጨዋታ ደቡብ አፍሪካና አዲስ አበባ ላይ በተደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ሁለት ቢጫ የማስጠንቀቂያ ካርድ የተመለከተውና አስራ አራት ቁጥር መለያ ለባሹ ምንያህል ተሾመ መሰለፉ ተገቢ አለመሆኑን ከማመኑም በላይ ለውድድሩ አዘጋጅ ይግባኝ እንደማይጠይቅ መግለጹ የሚታወስ ሲሆን ይህንን የፌዴሬሽኑን ውሳኔ ተከትሎ ፊፋ ኢትዮጵያ ከቦትስዋና ጋር ያደረገችውን የመልስ ጨዋታ ለባለሜዳዋ ቦትስዋና ፎርፌ እንደሚሰጥና ፌዴሬሽኑም ስድስት ሺ የስዊዝ ፍራንክ ቅጣት እንደሚጥልበት ይጠበቃል። ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ «ችግሩን ፈጥረዋል» ያላቸውን አካላት በደረጃ ከማሳወቁም በላይ እርምጃ ወስዶ ለሕዝብ እንደሚያሳውቅ በገለጸው መሠረት ነው አቶ አሸናፊ እጅጉን ያሰናበተው። በተጨማሪም እየተካሄደ ባለው ጉባኤ የፌዴሬሽኑ ምክትል ፕሬዘዳንት አቶ ብርሀኑ ከበደ ራሳቸውን ከኃላፊነት ሲያነሱ ሥራ አስፈፃሚውም የአቶ ብርሃኑን ውሳኔ እንዳጸደቀላቸው የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች አስታውቀዋል።

Previous Story

Sport: ፈርጉሰን ጠንካራ ቡድን ትተው አልፈዋል? እያጠያየቀ ነው

Next Story

አቶ ገብረመድህን አርአያ የዘማናችን አሉላ አባ ነጋ ተብለው በከፍተኛ ክብር ተሰየሙ

Go toTop