የኢትዮጵያ እስር ቤቶች ከሕሊና እስረኞች ነጻ መሆን አለባቸው !

April 29, 2014

የኢህአዴግ ፖለቲካ ዜጎችን የማሰር፣ ዜጎችን የማሸበር ፖለቲክ ነው። በቅርቡ በዞን ዘጠኞችና ጋዜጠኖች ላይ እየተፈጸመ ያለው ግፍ የሚያሳየው፣ አገዛዙ ሃሳብን በሃሳብ መመከት ሲሳነው የሃይል እርምጃ ለመዉሰድ ወደ ኋላ የማይል መሆኑን ነው።

ኢሕአዴግ ሽብርተኝነትን ለመከላከል ሳይሆን፣ ሰላማዊ ዜጎችን ለማሸበር ሲል ያወጣዉ የጸረ-ሽብርተኝነት ሕግ እንዲሰረዝ በመጠየቅ፣ የሚሊዮኖች ድምጽ ንቅናቄ ማድረጉ ይታወሳል። በአገሪቷ ክፍሎች ያሉ ሚሊዮኖች፣ አገዛዙ ዜጎችን በማሸበር እንዲያቆም ቢጠይቁም፣ አገዛዙ፣ የሕዝብን ጥያቄ በመናቅ ፣ አሁንም ኢትዮጵያውያን እየታሰሩ ናቸው። አሁንም የግፍ ቀንበር በሕዝባችን ላይ እየተጨነ ነው።

የአንድነት አባላት፣ ዜጎች ሃሳባቸውን በነጻነት በመግለጻቸው የማይታሰሩባት ኢትዮጵያን ለመገንባት፣ የታሰሩት ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ ለማድረግ ይታገላል። በተለያዩ እስር ቤቶች የታሰሩ ወገኖቻችን፣ አገዛዙ እንደሚለው ሽብርተኞች ሳይሆኑ ፣ «ለመብታቸው፣ ለነጻነትናቸውና ለአገራቸው ክብርና አንድነት የቆሙ፣ ብርቅዬ የኢትዮጵያ ጀግኖች ናቸው» ብሎ ነው የሚያምነው።

የታሰሩ እስረኞችን ለማበረታታት፣ ለነርሱም መፈታት አንድነት ያለዉን ቁርጠኝነት ለማረጋገጥ፣ ሚያዚያ 19 ቀን 2006 ከፍተኛ የአንድነት አመራር አባላት በሶስት እስር ቤቶች (ቃሊቲ፣ ቂሊንጦና ዝዋይ) አመርተው ነበር።

የአንድነት ሊቀመንበር ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው፣ አቶ አስቻለው እና አቶ አክሉ ግርግሬ በቃሊት እስክንደር ነጋ፣ ርዮት አለሙን እና አንዱዋለም አራጌን ለመጎነብኘት የሄዱ ሲሆን፣ ርዮት አለሙን እና እስክንደር ቢያገኙም አንድዋለምን ማነጋገር አትችሉም ተብለዉ ተመልሰዋል። ርዮት አለሙ፣ በአካል ጤንነቷ በጥሩ ሁኔታ ላይ ባይገኝም፣ በመንፈሷ ግን በጣም ትልቅ ጥንካሬ እንደሚታይበት ለማረጋገጥም ችለዋል።

በአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሃፊ፣ አቶ ስዩም ነገሻ የሚመራ ቡድን ደግሞ ወደ ቂሊንጦ እሥር ቤት ነበር ያመራው። ከአቶ ስዩም ጋር የአዲስ አበባ የአንድነት ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ዘካርያስ የነበሩ ሲሆን፣ በዚያም የታሰሩ ሰላማዊ የሙስሊም ችግር መፍተሄ አፍላላጊ ኮሚቴ አባላትን አግኝተው አነጋግረዋል።

የአንድነት ሁለቱ ሊቀመናብርት አቶ ተክሌ በቀለን እና አቶ በላይ በፍቅዱን፣ የድርጅት ጉዳይ ሃላፊው አቶ ዳንኤል ተፈራን፣ የሕዝብ ግንኙንተ ክፍል ሃላፊው አቶ ሃብታሙ አያሌውን፣ ደራሲና የአንድነት ደጋፊ አቶ አስራት አብርሃ ያቀፈ ወደ ሃያ የሚጠገ የአንድነት አባላትና ደጋፊዎች ቡድን ፣ ወደ ዝዋይ በማምራት በዚያ ከሚገኙ በርካታ እስረኞች ጋር ሰፊ ዉይይት አድርጓል። ናትናኤል መኮንን፣ አንድዋለም አያሌው፣ ዉብሸት ታዬ፣ ጀነራል አሳምነው፣ ሻምበል የሺዋስ፣ በቀለ ገርባ፣ ኦልባና ለሌሳ፣ አበበ ቀስቶ ..እንዲሁም በርካታ እስረኞች ለማነጋገር ተችሏል።

«እኛ በአካል ብንታሰርም፣ በመንፈሳችን ነጻ ሰዎች ነን። ነጻነት ያለ ትግል፣ ነጻነት ያለ ዋጋ አይገኝም። እኛ ዋና እየከፈልን ያለነው ለነጻነትና ለኢትዮጵያ ነው። ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከፍርሃት፣ ከዝምታ፣ ከራስ ወዳድነት ተላቆ የድርሻዉን ለማበርከት ይዘጋጅ» ሲሉም፣ የሕሊና እስረኞች፣ ለኢትዮጵያውያን መልክት አስተላልፈዋል።

የአንድነት ፓርቲ የፊታችን ሚያዚያ 26 ቀን በአዲስ አበባ የ«እሪታ ቀን» በሚል ሰላማዊ ሰልፍ እንደጠራ ይታወቃል። በዚህ ሰልፍ ከዉሃ፣ መብራት፣ ትራንስፖርት ችግር በተጨማሪም፣ በቃሊቲ፣ በቂሊንጦና በዝዋይ ለታሰሩ ጀግኖቻችን፣ እንዲሁም በቅርቡ ደግሞ የአገዛዙ የግፍ በትር ላረፈባቸውና በማእከላዊ ለሚገኙት ለዞን ዘጠኝ ወጣቶችና ጋዜጠኞች ያለንን አጋርነት የምንገልጽበት አጋጣሚ ተመቻችቷል።

ኑ ፣ እንነሳ ! ድምጻችንን እናሰማ ! የግፍ አገዛዝ በቃን እንበል ! ከሚሊዮኖች አንዱ እንሁን !

Previous Story

የእሪታ ቀን — እሁድ ሚያዝያ 26 ቀን ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት መነሻ ቀበና መድኃኔዓለም ከሚገኘው የአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት

Next Story

እነ ሚሚ ስብሃቱ የሚያጨሱት ምኑን ነው?

Go toTop