የጠገዴ ወረዳ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ዛሬ እንዳስታወቀው አቶ ቀናው አበጀ የተባለው ግለሰብ በፈጠረው ወሬ አካባቢው ተሸብሮ ሰንብቶ ነበር፡፡ በጠገዴ ወረዳ ‹‹እርጎየ›› ቀበሌ ነዋሪ የሆነው ይህ ግለሰብ ሕዳር 21 ቀን 2011 ዓ.ም ‹‹ከሌሊቱ 8፡00 ገነት ደርሸ ተመልሻለሁ፤ ሕዝቡ ሰኞ ቀን እንደሚጠፋም ፈጣሪ ነግሮኛል›› በሚል በማኅበረሰቡ ላይ መደናገርን ከፍተኛ መደናገጥን ፈጥሮ ቆይቷል፡፡ የኮሙኒኬሽን ፅ/ቤቱ እንደገለፀው ግለሰቡ ‹‹ገነት ስገባ የጸሎት መጽሐፍ ይዤ ነበር፡፡ በገነት ፈጣሪን ከአንዲት ሴት ጋር አግንቸዋለሁ፤ እሷም ማሪያም ትመስለኛለች›› ብሏል፡፡ በተጨማሪም ‹‹ይዤው ገነት ገባሁ›› ያለውን የጸሎት መጽሐፍ ፈጣሪ ተቀብሎ ‹‹ሕዝቡ ሰኞ ዕለት ይጠፋል›› ብሎ እንደነገረው በአደባባይ መናገሩ ታውቋል፡፡ በየትኛው ሰኞ ዕለት ሕዝቡ እንደሚጠፋ ባይታወቅም ‹‹በማኅበረሰቡ ዘንድ ሽብር ፈጥሯል›› በሚል አቶ ቀናው በቁጥጥር ስር መዋሉን ፅ/ቤቱ አስረድቷል፡፡
ግለሰቡ ገነት ደርሶ መምጣቱን እና ሕዝብ የሚያልቅ መሆኑን በእምነት እና በትምህርት ተቋማት አውጇል፡፡ አቶ ቀናው በፈጠረው ሽብር ምክንያትም ለተወሰኑት ቀናት ተማሪዎች ትምህርታቸውን አቋርጠዋል፤ ነዋሪዎችም በስጋት አካባቢውን ለቀዋል ብሏል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤቱ፡፡ በመሆኑም የሀሰተኛ ወሬ በመንዛት በማኅበረሰቡ ላይ ችግር በመፍጠሩ ግለሰቡ በቁጥጥር ስር ውሎ ምርመራ እየተደረገ መሆኑን ገልጿል፡፡
https://youtu.be/fabcQQpKeQU