በወልቃይት ምሽግ እየተቆፈረ ነው፣ መሳሪያ እየገባ ነው

November 5, 2018

በአዲስ አበባ ታትሞ ለንባብ የበቃው ግዮን መፅሄት ‹‹በወልቃይት ምሽግ እየተቆፈረ ነው፣ መሳሪያ እየገባ ነው›› ሲል ገለፀ፡፡ መፅሄቱ ከወልቃይትና ሁራ አካባቢ ተፈናቅለው በአዲስ አበበባ አብን ቢሮ የተጠለሉትን ግለሰቦች አነጋግሮ ነበር፡፡ አቶ አዳነ እሸቴ የተባሉት ከዳንሻ የተፈናቀሉት ግለሰብ ሲናገሩ ‹‹ወደእዚህ የመጣነው በአማራነታችን፣ በማንነታችን የሚደርስብንን በደል መፍትሄ ይሰጡናል ብለን ለምናያቸው የአገሪቱ መሪዎች ለማድረስ ነው፡፡›› ብለዋል፡፡ ጨምረውም ‹‹እኛ ሰላማዊ ሰዎች ነን፡፡ ሁካታ ለመፍጠር ፈልገን አይደለም ወደዚህ የመጣነው ተሰደን ነው›› የተናገሩት አቶ አዳነ አማራ በመሆናቸው እየተሰቃዩ እንደሆነና አሁንም ግፉ እንደቀጠለ አስረድተዋል፡፡ ህወሃት ከወልቃይት ውስጥ የተፈናቀለ ሰው የለም፣ የጠፋ ሰው የለም እያለ እየካደ መሆኑን ያወሱት እኚህ ግለሰብ ‹‹እኛ ግን ይኸው እንደምታዩን በችግር ምክንያት ቤተሰባችንን ጥለን ተሰደናል›› ብለዋል፡፡
‹‹ጠቅላይ ሚኒስትሩን ወይንም ምክትላቸውን ካላገኘን ሳምንትም ቢሆን ከዚህ ንቅንቅ አንልም፡፡ ተመልሰን ብንሄድ የሚጠብቀን ሞት ስለሆነ፣ የምንሞት ከሆ ህዝብ እያየን ህይወታችን ቢያልፍ ይሻለናል›› ያሉት አቶ ኣዳነ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ወይም ምክትላቸው አቶ ደመቀ ሰላማቸውን እንዲያስጠብቁላቸው ተማፅነዋል፡፡
አቶ አበበ ወርቁ የተባሉ ተፈናቃይ በበኩላቸው ከፀገዴ ወራ መምጣታቸውን ገልፀው ወልቃይት ለ7500 ዘመን በጎንደር አውራጃ ስር ትተዳደር እንደነበር ታሪክን አጣቅሰው አስረድተዋል፡፡ ወላጆቻቸው ይህንን ታሪክ ሲነግሯቸው እንደነበርና ወያኔ ወደስልጣን ከመጣ በኋላ ግን ወደ ትግራይ መካለላቸውን ገልፀው ይሄን የተቃወሙ እየታፈኑ መገደላቸውን ተናግረዋል፡፡ ጨምረውም ‹‹የእኔም አያት ወልቃይት የትግራይ አይደለም በማለቱ ተገድሏል›› ብለዋል፡፡ አቶ አበበ በመግለጫቸው የህወሃት ባለስልጣናት ‹‹መደመር ከፈለጋችሁ ከእኛ ጋር ሆናችሁ ነው እንጂ ዶ/ር አብይን መደገፍ አትችሉም፡፡ እሱ ትክክለኛ መሪ አይደለም፡፡ የመለስን ራእይ ያልያዘ ሰው ነው›› እያሉ ጭቆናና በደል እንደሚያደርሱባቸው ጠቅሰዋል፡፡
ወይዘሪት ፍሬ ይደግ ደግሞ ‹‹ሴቶች ባሎቻቸው እየታሰሩ፣ እነሱም እየተደፈሩ ነው›› ያለች ሲሆን ነዋሪነቷም ወልቃይት እንደሆነ ተናግራለች፡፡ ስለሁኔታው ስታስረዳም ‹‹ህፃናት በጣም አስጊ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ነው ያሉት፡፡ ትምህርት ቤት ውስጥ እየተማሩ ያሉ ልጆች ደብተራቸው ላይ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ፎቶ ካለበት አስተማሪው ተቀብሎ ይቀደዋል፣ደበድበዋል›› ብላለች፡፡ በተመሳሳይ ከወልቃይት ወረዳ የመጣችው ወይዘሪት አዳኑ ጥላሁን ‹‹በወልቃይት በዚህ ሰአት ጨርሶ ሰላም የለም፡፡›› ካለች በኋላ በንግድ ስራ የሚተዳደሩ በአካባቢው የአማርኛ ዘፈን እንዳይከፍቱ መከልከላቸውን አስረድተዋል፡፡

ኮፎ ጌታቸው የሚባል ወጣት በበኩሉ ‹‹አሁን በወልቃይት ምሽግ እየተቆፈረ ነው፡፡ ሚልሻው በከፍተኛ ሁኔታ እየታጠቀ ከየት እንደመጣ ልታወቀ ቦምብ መሳሪያ በብዛት እየገባ ነው ያለው፡፡ ይሄ ግልፅ ነው፡፡ ከበፊቱ በበለጠ የወልቃይትን ህዝብ ለመጨፍጨፍ እንደታሰበ አማራውን ለማጥቃት ዝግጅት እየተደረገ እንደሆነ ይታያል›› ሲል ለጊዮን መፅሄት ተናግሯል፡
https://www.youtube.com/watch?v=urrQCDkbbQE&t=489s፡

Previous Story

የባህል ማዕከል በፌዴራል ፖሊስ አባላት ላይ ክስ መሰረተ

Next Story

ታሪካዊው የቴዲ አፍሮ ኮንሰርት በአዲስ አበባ ተካሄደ

Go toTop