በቦጋለ አበበ
አትሌት አበሩ ከበደ በጃፓን ዋና ከተማ የተካሄደውን የቶኪዮ ማራቶን አሸነፈች።አበሩ በውድድሩ ከጃፓንና ኬንያ አትሌቶች ጠንካራ ፉክክር ቢገጥማትም በአስደናቂ ብቃትና ፍጥነት መርታት ችላለች።
የአበሩ ዋነኛ ተፎካካሪዎች ኬንያዊቷ ካሮሊን ኪሌልና ጃፓናዊቷ አዙሳ ኖጂሪ በተለይም በመጀመሪያዎቹ አምስት ኪሎ ሜትሮች ከባድ ፈተና ቢሆኑባትም አበሩ ከአሥር ኪሎ ሜትር በኋላ የበላይነቷን አሳይታለች።
አበሩ በመጀመሪያዎቹ አምስት ኪሎ ሜትሮች ከኬንያዊቷ ካሮሊንና ጃፓናዊቷ አዙሳ ጎን ለጎን በመሮጥ በ 16፡48 ሰዓት ርቀቱን ለማጠናቀቅ በቅታለች። ቀጣዮቹን አምስት ኪሎ ሜትሮች ሦስቱ አትሌቶች በአንድ ላይ ሆነው በ33፡31 ሰዓት አገባድደዋል።
ውድድሩ አሥራ ሰባተኛ ኪሎ ሜትር ላይ ሲደርስ ጃፓናዊቷ አዙሳ ከአበሩ ና ካሮሊን ወደ ኋላ ቀርታለች።አበሩ ከኬንያዊቷ ጋር ብዙም ኪሎ ሜትር ሳትሮጥ ካሮሊንን አዳክማ ውድድሩን ለብቻዋ መርታለች።
አሥራ ሰባተኛውን ኪሎ ሜትር ላይ አበሩ ቢያንስ በአሥራ ስድስት ሰከንዶች ከኋላዋ ስትከተላት የነበረችው የሀገሯ ልጅ የሺ ኢሳያስ ውድድሩ ግማሽ ያህል ሲቀረው ደርሳባት አሥር ያህል ኪሎ ሜትር አብራት ሮጣለች።ከዚያም በኋላ አበሩ ፍጥነቷን ጨምራ በመሮጥ ርቀቱን በ 2፡25፡34 ፈፅማለች።አበሩ ውድድሩ ሊጠናቀቅ ጥቂት ኪሎ ሜትሮች ሲቀሩት ጠንካራ ተፎካካሪ ቢገጥማት የቦታውን ክብረወሰን የማሻሻል አቅም እንደነበራትም ውድድሩን ስትፈጽም የነበራት ጉልበት ምስክር ሆኗል።
«በውድድሩ ከሠላሳ ሰባተኛ እስከ አርባ አንደኛ ኪሎ ሜትር ድረስ በፍጥነት ለመሮጥ የማያመች ንፋስ ነበር፤ከከባድ ንፋስ በተጨማሪ ውድድሩ ዳገታማ መሆኑ ክብረወሰን እንዳሻሽል አላደረገኝም»በማለት አበሩ አስተያየቷን ሰጥታለች።
ከአበሩ ጋር ከአሥር ኪሎ ሜትር በላይ ጥሩ ፉክክር ያሳየችው የሺ አበሩን እስከ መጨረሻ መፎካከር ባትችልም ሁለተኛ ሆና ውድድሯን ፈፅማለች።የሺ ርቀቱን ያጠናቀቀችው በ2፡26፡01 ሰዓት ነው።የአርባ ዓመቷ ጀርመናዊት ኢሬና ሚኪቴንኮ የአሸናፊነት ግምት ሳይሰጣት በ2፡26፡41 ሰዓት ሦስተኛ በመሆን ውድድሯን አጠናቅቃለች።
ባለፈው ዓመት የናጎያ ማራቶን ሻምፒዮኗ አልቢና ማዮሮቫ በእዚህ ውድድር አራተኛ በመውጣት ውድድሩን አጠናቅቃለች።አልቢና ርቀቱን የፈፀመችው 2፡26፡51 በሆነ ሰዓት ነው።ጃፓናዊቷ ዮሺሚ ኦዛኪ በ2፡28፡30 አምስተኛ መሆን ችላለች።
እ.ኤ.አ በ2009 የዓለም ሻምፒዮና ላይ የነሃስ ሜዳሊያ ባለቤት የነበረችው ጃፓናዊቷ ኦዛኪ በዘንድሮው የቶኪዮ ማራቶን ጥሩ ጀረጃ በመያዝ ውድድሯን ያጠናቀቀች ብቸኛዋ ጃፓናዊት ነች።«አስቸጋሪ ንፋስ ባይኖረ ጥሩ ልሮጥ እችል ነበር»በማለት ኦዛኪ አስተያየት ሰጥታለች።
በተመሳሳይ በወንዶች በተካሄደው ውድድር ኬንያዊው ዴኒስ ኪሚቶ አዲስ ክብረወሰን በማስመዝገበ ጭምር ነው ያሸነፈው።ኪሚቶ ርቀቱን በ2፡06፡50 ነው የፈፀመው።ኪሚቶ ያሸነፈበት ሰዓት አዲስ የቦታው ክብረወሰን ሆኖ ተመዝግቧል።
ኪሚቶ ባለፈው መስከረም በበርሊን ቢኤም ደብሊው ማራቶን ድንቅ ብቃቱን በማሳየት ያሸነፈ አትሌት ነው።ኪሚቶ ፈጣን ሰዓት ያስመዘገበው አስቸጋሪ የነበረውን ንፋስ የመቋቋምና የሀገሩን ልጆች ጄምስ ዋምባይንና በርናንድ ኪፕዬጎን የመሳሰሉ አትሌቶችን በመቋቋም ጭምር መሆኑ ድሉን የተለየ አድርጎታል።
ኪሚቶ የውድድሩን ግማሽ ያገባደደው በ1፡04፡22 ሲሆን ይህም እገባበታለሁ በሎ ካቀደው ሁለት ደቂቃ ያህል የዘገየ ነበር።
ኪሚቶ እስከ ውድድሩ ሃያ ስምንተኛ ኪሎ ሜትር ድረስ ከሀገሩ ልጆች ጄምስ ዋምባይ፤በርናንድ ኪፕዬጎና ጂልበርት ኪርዋ ጋር ጎን ለጎን በመሮጥ ብቃቱን በሚገባ አስመስክሯል። ሦስቱ አትሌቶች በተለይም ሠላሳኛ ኪሎ ሜትር ላይ አሸናፊውን ለመለየት በሚያስቸግር ዓይነት ሁኔታ ያሳዩት ጠንካራ ፉክክር ለውድድሩ ልዩ ግምት ሰጥቶታል።
ሠላሳኛ ኪሎ ሜትሩ መገባደጃ ላይ ኪሜቶ ውድድሩን ከፊት በመመራት ውድደሩን ፈጣን እንዲሆን ሲያደርገው ኪፕዬጎ በአምስት ሰከንድ ዘግይቶ ሲከተለው ቆይቷል። ኪሜቶ በአስደናቂ ፍጥነት ከሠላሳ አምስት እስከ አርባ ያለውን ኪሎ ሜትር ያገባደደው በ14፡35 ሰዓት ሲሆን ኪሚቶ ውድድሩን ሊያጠናቅቅ ከሁለት ኪሎ ሜትር ያነሰ ርቀት እስኪቀረው ድረስ ኪፕዬጎ በቅርበት ተፎካክሮታል።
ኪሚቶ ኪፕዬጎን አስከትሎ በመሮጥ ጥንቃቄ የተሞላበት ፉክክር አድርጎ ከአርባ ኪሎ ሜትር እስከ መጨረሻ ያሉትን ሁለት ኪሎ ሜትሮች በ6፡34 ደቂቃ በማጠናቀቅ ውድድሩን በቀዳሚነት ፈፅሟል።ይህም ቀድሞ ተመዝግቦ የነበረውን የቦታውን ክብረወሰን በ ሠላሳ ሦስት ሰከንድ እንዲያሻሽል አስችሎታል።
«ሠላሳ አምስተኛ ኪሎ ሜትር ላይ ውድድሩን የማሸነፍ አቅም እንዳለኝ አወቅሁ፤ የውድድሩ መሪ መፍጠን ስላለቻለ ከፊት ከፊት ለመመራት አስቤ ነበር ነገርግን ኪሎ ሜትሩ ገና ስለሆነ ተውኩትና ከኋላ ሮጥኩኝ፤ይህም ትንፋሽ ሰብስቤ መጨረሻ ላይ በፍጥነተ እንድሮጥ አስችሎኛል» በማለት ኪሚቶ አስተያየት ሰጥቷል።
ኪሚቶ ከውድድሩ በኋላ ለዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ማህበር ድረ ገፅ እንደተናገረው፤ በቀጣዩ የዓለም ሻምፒዮና ላይ ውድድር ይፈልጋል።ይህ ካልሆነም በበርሊን ማራቶን የዓለምን የማራቶን ክብረወሰን የማሻሻል ፍላጎት አለው።
በውድድሩ እስከ አርባኛው ኪሎ ሜትር እልህ አስጨራሽ ፉክክር ያደረገው ኪፕዬጎ ሁለተኛ ሆኖ ውድድሩን ፈፅሟል።ኪፕዬጎ ርቀቱን ለመፈፀም 2፡06፡58 የወሰደበት ሲሆን ይህም የራሱ ምርጥ ሰዓት ሆኖ ተመዝግቦለታል።
እስከ ሃያ ስምንተኛው ኪሎ ሜትር ጠንካራ ተፎካካሪ የነበረው በርናንድ በ2፡07፡53 ሰዓት ሦስተኛ ሆኖ ውድድሩን በማጠናቀቅ ኬንያውያን በውድድሩ የበላይነት ይዘው እንዲያጠናቅቁ አስችሏል።
በርካታ ጃፓናውያን በቴሌቪዝን መስኮትና በሬዲዮ ከመከታታል ባሻገር ውድደሩ በሚካሄድባቸው ጎዳናዎች ድጋፋቸውን ሲሰጡት የነበረው ጃፓናዊው ካዙሂሮ ማኤዳ አራተኛ በመውጣት ውድድሩን ፈፅሟል።ማኤዳ በተለይም በመጀመሪያዎቹ አሥር ኪሎ ሜትሮች ጠንካራ ፉክክር ካደረጉ አትሌቶች አንዱ ነበር።
ማኤዳ ርቀቱን ለመፈፀም 2፡07፡59 ወስዶበታል።ማኤዳ አራተኛ ሆኖ ያጠናቀቀው ኬንያዊው ዋምባይንና ኢትዮጵያዊው ፈይሳ በቀለን በመጨረሻዎቹ ኪሎ ሜትሮች ተፎካከሮ ነው።«2፡07 በሆነ ሰዓት ውድድሩን እፈፅማለሁ የሚል ግምት አልነበረኝም፤ ከባድ ንፋስ ውድድሩን አስቸጋሪ አድርጎትም ያስመዘገብኩት ሰዓት አስደስቶኛል»በማለት ማኤዳ አስተያየቱን ሰጥቷል።
ኬንያዊው ዋምባይ በ2፡08፡02 አምስተኛ ደረጃን ይዞ ሲያጠናቅቅ ኢትዮጵያዊው ፈይሳ በቀለ በ2፡08፡17 ሰዓት ስድስተኛ ሆኗል።