በኦሮሚያ እና ሲዳማ ክልል አዋሳኝ ቦታዎች በተቀሰቀሰ ጥቃት ቢያንስ አምስት ሰዎች ተገደሉ

April 5, 2022

በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ አርሲ ዞን እና በሲዳማ ክልል አዋሳኝ ቦታዎች ላይ ከትላንት በስቲያ እሁድ መጋቢት 25 ምሽት በተቀሰቀሰ ግጭት ቢያንስ አምስት ሰዎች መገደላቸውን የሲዳማ ክልል የሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። በግጭቱ በጥይት ከቆሰሉ አስራ አምስት ሰዎች ውስጥ ሶስቱ የደረሰባቸው ጉዳት “ከባድ” የሚባል እንደሆነ የህክምና ባለሙያዎች አስታውቀዋል።

የእሁዱ ግጭት የተቀሰቀሰው፤ በሲዳማ ክልል፣ ጪሪ ወረዳ፣ ሀሌላ ቀበሌ ነዋሪዎች ዘንድ ታዋቂ የሆኑ የሀገር ሽማግሌ መገደላቸውን ተከትሎ እንደሆነ አቶ አለማየሁ ገልጸዋል። አዴ ሎኬ ዮኔ የተባሉት እኚሁ አባት ከትላንት በስቲያ ምሽት አራት ሰዓት ገደማ የተገደሉት “ለጊዜው ማንነታቸው ባልታወቁ ታጣቂዎች ነው” ብለዋል።

ይህ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ በሀሌላ ቀበሌ የተቀሰቀሰው ግጭት ወደ አጎራባች ቀበሌዎች መስፋፋቱን አቶ አለማየሁ አስረድተዋል። ግጭቱ በሲዳማ ክልል፣ ጪሪ ወረዳ ስር የምትገኘውን ሱጫ ቀበሌን እንደዚሁም በኦሮሚያ ክልል ሻምበል እና ውሮ ቀበሌዎችን ማዳረሱን አመልክተዋል። በአካባቢዎቹ የተፈጠረውን ክስተት “ሁከት” ሲሉ የጠሩት የሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ ቢሮ ኃላፊው፤ “የብሔር መልክ እንዲይዝ የተደረገ ሙከራ” እንደነበርም ጠቁመዋል።

በግጭቱ እስካሁን ከሲዳማ ክልል በኩል የሀገር ሽማግሌውን ጨምሮ ቢያንስ ሁለት ሰዎች ሲገደሉ፤ በኦሮሚያ በኩል ደግሞ የሶስት ሰዎች ህይወት እንዳለፈ አቶ አለማየሁ ገልጸዋል። በሲዳማ ክልል፣ ቦና ዙሪያ ወረዳ ስር ያለው የቦና አጠቃላይ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ አቶ መንገሻ ቦኮ በግጭቱ በጥይት የቆሰሉ ሰባት ሰዎች ወደ ሆስፒታላቸው መምጣታቸውን ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

ቆስለው ለህክምና እርዳታ ወደ ሆስፒታሉ ከመጡት ሰዎች ውስጥ የተወሰኑት ግጭቱ የተቀሰቀሰበት የጪሬ ወረዳ ነዋሪ መሆናቸውን የሚናገሩት የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ፤ ሌሎቹ ተጎጂዎች በበንሳ ወረዳ ስር ባሉት ቀጠና፣ ከራሞ እና ሀማሾ ቀበሌዎች እንዲሁም የዳኤላ ወረዳ፣ ኤቻማ ቀበሌ ነዋሪዎች መሆናቸውን አስረድተዋል። ከእነዚህ ተጎጂዎች መካከል ሶስቱ በከባድ ሁኔታ በመጎዳታቸው ወደ ሐዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል መላካቸውን አቶ መንገሻ አክለዋል።

ኢትዮጵያ ኢንሳይደር

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

ደቡብ፣ ቤንሻንጉል፣ አፋርና ሱማሌ እኛን የመገዳደር አቅም ስለሌላቸው በቀላሉ እንቆጣጠራቸዋለን!

Next Story

ግሩም ጫላ ጋዜጠኝነትን መሸቀጫ ያደረገ የአብይ አህመድ ካድሬ

Go toTop