የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ከኃላፊነታቸው ለቀቁ – አቶ ግርማ ዋቄ፤ እንዲመሩ ተሾሙ

March 23, 2022

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም ከኃላፊነታቸው በገዛ ፍቃዳቸው ለቀቁ፡፡ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ምንጭ አቶ ተወልደ የስራ መልቀቂያ ማስገባታቸውን አረጋግጠዋል፡፡ እኒሁ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ምንጭ ዋና ስራ አስፈጻሚው በገዛ ፍቃዳቸው ከስራ መልቀቃቸውን ዛሬ ከሰዓት ለመስሪያ ቤቱ ሰራተኞች ከተሰራጨ ኢሜይል እንዳወቁ ጨምረው ገልጸዋል፡፡
አቶ ተወልደ የኢትዮጵያ አየር መንግድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሆነው የተሾሙት በጥር 2003 ዓ.ም ነበር፡፡ አቶ ተወልደ ለ11 ዓመታት በዋና ስራ አስፈጻሚነት የመሩትን ተቋም የተቀላቀሉት ከ37 ዓመታት በፊት በ1977 ዓ.ም ነው፡፡
በአየር መንገዱ በትራንስፖርት ወኪልነት ስራ የጀመሩት አቶ ተወልደ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል፡፡ ከእንግሊዙ ኦፕን ዩኒቨርሲቲ ደግሞ በበቢዝነስ አስተዳደር የማስተርስ ዲግሪያቸውን ተቀብለዋል፡፡ አቶ ተወልደ በ2011 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ መቀበላቸው ይታወሳል፡፡

አቶ ግርማን በአዲሱ የኃላፊነት ቦታ ላይ በቅርቡ የመደባቸው የመንግስት የልማት ድርጅቶች ይዞታ አስተዳደር መሆኑን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ማምሻውን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

አቶ ግርማ “ከፍተኛ ልምድ ያላቸው፣ ስኬታማ እና ከበሬታ ያላቸው የቢዝነስ መሪ” መሆናቸውን የገለጸው አየር መንገዱ፤ በአቪዬሽን ኢንዱስትሪውም በቅጡ የሚታወቁ ግለሰብ መሆናቸውን አመልክቷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድን በመሩባቸው ዓመታት፤ ተቋሙ ላስመዘገበው ፈጣን እና ትርፋማ እድገት መሰረት የጣሉ መሆናቸውን ለዚህ ገለጻው በማሳየነት ጠቅሷል።

“የአቶ ግርማ የውሳኔ አሰጣጥ ክህሎት የተፈተነ እና በሚገባ የተረጋገጠ ነው” ያለው አየር መንገዱ፤ “የእርሳቸው ልምድ፣ የስራ ባህል እና ትጋት ሲቀናጅ፤ ቦርዱን በሊቀመንበርነት ለመምራትም ሆነ አየር መንገዱን ወደ ቀጣይ ደረጃ ለማሻገር ብቁ ያደርጋቸዋል” ሲል የቀድሞው ዋና ስራ አስፈጻሚ ወደ ተቋሙ መመለስ የሚኖረውን ጠቀሜታ አስገንዝቧል።

ከታህሳስ 2007 ዓ.ም ጀምሮ የኢትዮጵያ አየር መንገድን በቦርድ ሊቀመንበርነት ሲመሩ የቆዩት የቀድሞው የተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ አባዱላ ገመዳ ናቸው። አቶ አባዱላ የሊቀመንበርነት ቦታውን የተረከቡት ከቀድሞው የብአዴን ሊቀመንበር እና የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አዲሱ ለገሰ እንደነበር ይታወሳል።

አየር መንገዱ በዛሬው መግለጫው የዋና ስራ አስፈጻሚው ተወልደ ገብረማርያምን ከስራ መልቀቅ አረጋግጧል። አቶ ተወልደ ላለፉት ስድስት ወራት በአሜሪካ በህክምና ላይ መቆየታቸውን የገለጸው አየር መንገዱ፤ በግል የጤና ሁኔታዎች ላይ ማተኮር ስለሚገባቸው በኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚነት መቀጠል አለመቻላቸውን አስረድቷል።

ይህን ተመርኩዞም አቶ ተወልደ ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ አስተዳደር ቦርድ በጡረታ ለመሰናበት ጥያቄ ማቅረባቸውን አመልክቷል። ቦርዱ ዛሬ ረቡዕ መጋቢት 14፤ 2014 ባደረገው መደበኛ ስብሰባ አቶ ተወልደ ያቀረቡትን የቅድመ ጡረታ ጥያቄን እንደተቀበለ አየር መንገዱ አስታውቋል። የአየር መንገዱ ቦርድ የአቶ ተወልደን ተተኪ በቅርቡ እንደሚያስታውቅም ጨምሮ ገልጿል።

ኢትዮጵያ ኢንሳይደር

[በዚህ ዘገባ ላይ ተጨማሪ መረጃ ታክሎበታል]

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

ESAT INTERNATIONAL ከኢሳት ለምን ተለየን March 2022

Next Story

ሕዝብ ሆይ! በእርዳታና በምጽዋእት ስም የሚዘርፍህን ሌባ አስተፋው! ተማህበራዊ ግንኙነትም አርቀው!

Go toTop