ዘመም ይላል እንጂ (በእውቀቱ ስዩም )

March 13, 2022
እንደ ጊዜው መክፋት
እንደ ግፉ መስፋት
እንደ አገሩ ክስመት
እንደ አገሬው ጥመት
እንደ ሰው ጭካኔ እንደ ልቡ ፍሬ
ተዐምር ነው መትረፍሽ ተዐምር ነው መኖሬ።
.
የበጎ ሰው ሀሳብ ሲካድ ዕለት በዕለት
ጉድጓድ ተምሶለት
ስብዕና ሲቀበር
በዚህ ምድር መኖር አያስመኝም ነበር።
.
ምድር ሳር ቅጠሉ በስጋት ተሞልቶ
የማለዳው ሰማይ እንደ አንቀልባ ቀልቶ
ታረደ
ነደደ
ከዘብጥያ ወጥቶ ዘብጥያ ወረደ
የሚል ዜና ብቻ አየሩን ሲሞላው
ሰው በገዛ ጥላው በረግጎ ሲሸበር
በዚህ ምድር መኖር አያስመኝም ነበር።
.
አዎ
ለጊዜውም ቢሆን ግፍ ያደነዝዛል
በደል ያስተክዛል
ጊዜም ጠብን ሽሮ ወደፊት ይጓዛል
በልብ ሰሌዳ ላይ ቂም ይደበዝዛል።
በነገ ያመነ፣
ልጁን ቀብሮ መጥቶ ሚስቱን ያስረግዛል።
ይቅርታና ምህረት
ፍቅርና ህብረት
ከግፍ ጋር ፍልሚያቸው ሲሆን የሞት ሽረት
ዳገት ይወጣሉ በእንጥፍጣፊ አቅም
የመኖር ፍላጎት፣
ዘመም ይላል እንጂ ተገርስሶ አይወድቅም።
(በእውቀቱ ስዩም – አዳምኤል፣ ገጽ 34)

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተፈጸመው ሰውን የማቃጠል ድርጊት፤ የመንግስት የጸጥታ አባላት መሳተፋቸውን ማረጋገጡን ኢሰመኮ አስታወቀ

Next Story

የብልጽግና የምርጫ ሿሿና ጸረ ፋኖ ዘመቻው የት ያደርሳል? Hiber Radio Special Mar 13, 2022

Go toTop