የቅድሥት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎች ከትምህርት ማቆም አድማው በተጨማሪ የረሃብ አድማ ጀመሩ

March 24, 2013
አቡነ ማቲያስ

(ሪፖርተር) መጋቢት 4 ቀን 2005 ዓ.ም. የተቃውሞ ደብዳቤ ለፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ያቀረቡት የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎች፣ ላለፉት አሥር ቀናት ትምህርታቸውን ከማቆማቸውም በተጨማሪ፣ ከመጋቢት 12 ቀን 2005 ዓ.ም. ምሽት ጀምሮ የረሃብ አድማ ማድረጋቸው ዛሬ አዲስ አበባ ላይ ታትሞ የወጣው ሪፖርተር ጋዜጣ ዘገበ።

እንደሪፖርተር ጋዜጣ ዘገባ   ተማሪዎቹ ያቀረቡት የተቃውሞ ደብዳቤ ለአንድ ሳምንት ምላሽ ስለተነፈገው፣ መጋቢት 12 ቀን 2005 ዓ.ም. ፓትርያርኩ በሚያስቀድሱበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን፣ ልብስ ተክህኖ ለብሰው በመሄድ ቢጠብቋቸውም፣ ፓትርያርኩ ያለወትሮአቸው ሳይገኙ መቅረታቸውን ደቀ መዛሙርቱ ተናግረዋል፡፡
ከመልካቸው በስተቀር መጠሪያቸውና ማንነታቸው የማይታወቁ ግለሰቦች፣ አመልካች ጣታቸውን እየቀሰሩ ሊያስፈራሯቸው መሞከራቸውን የገለጹት ተማሪዎቹ ጥያቄያቸው ተገቢና አስፈላጊ በመሆኑ ምላሽ እስከሚሰጣቸው ድረስ የረሃብ አድማውንና ትምህርት ማቆማቸውን እንደሚገፉበት ተናግረዋል ያለው የጋዜጣው ዘገባ ፓትርያርኩን በጽሕፈት ቤታቸው ተገኝተው ለማነጋገር ለመጋቢት 6 ቀን 2005 ዓ.ም. በንቡረዕድ ኤልያስ አብርሃ በኩል ቀጠሮ ተይዞላቸው እንደነበር የገለጹት ተማሪዎቹ፣ በዕለቱ ለመግባት ሲሞክሩ “የሲኖዶስ አባላት ስብሰባ ላይ ናቸው” በማለት በጥበቃ ሠራተኞች መከልከላቸውን ተናግረዋል ብሏል።
ከኮሌጁ ኃላፊዎች ጋር ሊያወያዩአቸው ወደ ኮሌጁ የመጡ የጠቅላይ ቤተ ክህነትና የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ተማሪዎቹ ያነሷቸውን ጥያቄዎች በማቅረብ ከማወያየት ይልቅ፣ ለመሸምገል መሞከራቸው እንዳሳዘናቸው የገለጹት ተማሪዎቹ እነሱንና የኮሌጁን ኃላፊዎች ሊያስማሟቸው የሚችሉት ያነሷቸውን ጥያቄዎች በመመልከት መፍትሔ እንዲያገኙ ሲያደርጉ ብቻ መሆኑን አሳውቀዋል፡፡
ተማሪዎቹ ምግብ የማይበሉና ትምህርታቸውን የማይማሩ ከሆኑ የተሰጣቸውን ብርድ ልብስ፣ አንሶላና መታወቂያ አስረክበው የኮሌጁን ግቢ እንዲለቁ የኮሌጁ አስተዳደር ማስታወቂያ ማውጣቱ ግርምት እንደፈጠረባቸውም ገልጸዋል፡፡
ተማሪዎቹ ላቀረቧቸው ጥያቄዎችና በረሃብ አድማ ላይ ስለመሆናቸው ኮሌጁም ሆነ ቤተክህነት ምን እያደረጉ እንደሚገኙ ማብራሪያ እንዲሰጡን የኮሌጁ የበላይ ጠባቂ አቡነ ጢሞቲዎስን፣ የሥልጠናና ትምህርት ዋና ክፍል ኃላፊውን አባ ሠረቀንና የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ አቡነ ፊሊጶስን አግኝተን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካልንም ሲል ሪፖርተር ዘገባውን ቋጭቷል።

Previous Story

ሰላማዊ ትግል እና ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች – የማይረሳ ታሪክ በኢትዮጵያ ተሰራ! ከግርማ ሞገስ

Next Story

ብሔራዊ ቡድናችን ለብራዚሉ የዓለም ዋንጫ የሚያደርገውን ጉዞ እያሳመረ ነው

Go toTop