የአማራ እና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝደንቶች በቅርቡ የኦሮሞ ነጻነት ጦር የተባለውን ታጣቂ ቡድን “ለማጥፋት” ይወሰዳል ያሉት እርምጃ እንዲቆም የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ጠየቀ። ኦነግ ባወጣው መግለጫ ግጭቱ በሰላም እንዲፈታ ጥሪ አቅርቧል።
የአማራ እና የኦሮሚያ ክልል መሪዎች የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ ሹማምንት በተገኙበት በባሕር ዳር ከተማ ባለፈው ሰኔ 21 ቀን 2014 በሰጡት መግለጫ በታጣቂ ቡድኑ ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀው ነበር። ባለሥልጣናቱ መግለጫውን የሰጡት ሰኔ 11 ቀን 2014 በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ወረዳ ቶሌ ቀበሌ አሰቃቂ ጥቃት ተፈጽሞ በርካታ ሰዎች ከተገደሉ በኋላ ነው።
የኦሮሞ ነጻነት ጦር በኦሮሚያ ክልል ደምቢዶሎ እና ጊምቢ ከተሞች እንዲሁም በጋምቤላ ጥቃቶች ፈጽሟል።በጥቃቶቹ በበርካታ መቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰዎች፣ የጸጥታ አስከባሪዎች እና የአማጺ ቡድኑ አባላት ተገድለዋል። ባለሥልጣናቱ ከሰጡት መግለጫ በኋላ ኦነግ እንደሚለው በኃይል የታጠቁ ወታደሮች የጫነ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ቅፍለት ከአማራ ክልል በኩል በተለያዩ አቅጣጫዎች ወደ ኦሮሚያ ክልል ገብቷል።
የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ባወጣው መግለጫ ግን ቀውሱ በኃይል ይፈታል ብሎ እንደማያምን አስጠንቅቋል። “ለሚፈጠረው ተጨማሪ የደም መፋሰስ ተጠያቂ በመሪዎቹ ትከሻ ላይ እንደሚወድቅ” የገለጸው ኦነግ ሌሎች ክልሎች እጃቸውን እንዳያስገቡ ጠይቋል።
ምንሊክ ሳልሳዊ