የአውሮፓ ፉትቦል ፌዴሬሽን ድሮግባ ሕጋዊ ተጫዋች ነው አለ

March 2, 2013

ከቦጋለ አበበ
ኮትዲቯራዊው ኮከብ ዲዲየር ድሮግባ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለቱርኩ ክለብ ጋላታሳራይ ተሰልፎ መጫወቱ አግባብ መሆኑን የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ማረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ።
ድሮግባ በሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ ጋላታሳራይ ከጀርመኑ ሻልክ ዜሮ አራት ጋር ሲጫወት ተሰልፎ አንድ ግብ ከመረብ አሳርፏል።ይሁን እንጂ የጀርመኑ ክለብ ድሮግባ ለጋላታሳራይ ተሰልፎ የተጫወተው ህጋዊ ባልሆነ መንገድ ነው ሲል ለአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ይግባኝ ጠይቋል።
የሰላሳ አራት ዓመቱ ድሮግባ ሁለቱ ክለቦች አንድ ለአንድ በሆነ አቻ ውጤት በተለያዩበት የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ ለቱርኩ ክለብ ለመጫወት አልተመዘገበም በሚል ሻልክ ያቀረበው ጥያቄ በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ሲጣራ ቆይቶ ተጫዋቹ ለጋላታሳራይ የተጫወተበት መንገድ አግባብ እንደሆነ ተረጋግጧል።
ድሮግባ ባለፈው የፈረንጆች የካቲት ሃያ ቀን ሁለቱ ክለቦች ባደረጉት ጨዋታ ከቻይናው ክለብ ሻንጋይ ሽኑዋ በውሰት መጥቶ ሳይመዘገብ መጫወት የማይችል ቢሆንም ተጫዋቹ ከሃያ ቀን ቀደም ብሎ ለጋላታሳራይ የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ ለመሰለፍ መመዝገቡ ተረጋግጧል።
ጋላታሳራይ ድሮግባን በሻምፒዮንስ ሊግ አሰልፎ ማጫወቱ አግባብ ሆኖ ባይገኝ በጨዋታው ያገኘውን ነጥብ የመነጠቅ አደጋ ያጋጥመው ነበር።ይሁን እንጂ ክለቡ ጥፋተኛ ሆኖ ባለመገኘቱ በደርሶ መልስ የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ ከሻልክ ጋር በእኩል ነጥብ ይጫወታል።
በደቡብ አፍሪካ ዋንጫ ኮትዲቯርን የዋንጫ ባለቤት የማድረግ እድሉ የከሸፈበት ድሮግባ አሁንም በአውሮፓ ክለቦች ተፅዕኖ ፈጣሪነቱን እያስጠበቀ ይገኛል።በእንግሊዙ ቼልሲ ክለብ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን ባነሳ ማግስት እንግሊዝን ለቆ ዳጎስ ያለ ደመወዝ ወደሚከፍለው የቻይናው ክለብ ሻንጋይ ሽኑዋ አምርቷል።ከስድስት ወር ቆይታ በኋላም ከቻይናው ክለብ በውሰት ወደ ቱርኩ ጋላታሳራይ በማምራት ዳግመኛ የሻምፒዮንስ ሊግ ድምቀት ሆኗል።
ለሻንጋይ ሽኑዋ ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር ያህል ለመጫወት ተፈራርሞ የነበረው የኮትዲቯር የቁርጥ ቀን ልጅ ድሮግባ ወደ ኢስታንቡሉ ክለብ ጋላታሳራይ የመጣው ባለፈው ጥር ለአሥራ ስምንት ወር ያህል ለመጫወት ነው።
እ.ኤ.አ በ1978 መጋቢት ላይ የተወለደው ድሮግባ 2003 ላይ ለማርሴል ክለብ በሦስት ነጥብ ሦስት ሚሊዮን ዩሮ በመፈራረም በውድድር ዓመቱ አስራ ሰባት ግቦችን ከመረብ አሳርፏል።ክለቡን ለታላላቅ የአውሮፓ ጨዋታዎች በማብቃትም በእግር ኳስ ስሙን ማግነን ችሏል።
ድሮግባ 2004 ላይ ቼልሲን በሃያ አራት ሚሊዮን ዩሮ በመቀላቀል የፕሪሚየር ሊግ፤ሻምፒዮንስ ሊግ፤ሦስት ኤፍ ኤ ካፕና ሁለት የሊግ ካፕ ዋንጫዎችን ማንሳት ችሏል።ድሮግባ በእንግሊዝ ተፅዕኖ ፈጣሪ ተጫዋች በሆነበት ወቅት ሁለት ጊዜ ምርጥ አፍሪካዊ ተጫዋች በመሆን ተመርጧል።
ከቼልሲ ክለብ ጋር በርካታ ድሎችን በማጣጣም በዓለም ካሉ ታላላቅ የፊት መስመር ተጫዋቾች መካከል አንዱ መሆን የቻለው ድሮግባ ቼልሲን ከተሰናበተ በኋላም በቻይና ተወዳጅ ተጫዋች ሆኖ ሰንብቷል።አሁን ደግሞ በቱርኩ ታላቅ ክለብ በመሰለፍ እያሳየው ያለው ድንቅ ችሎታ የስፖርት ቤተሰቡ መነጋገሪያ ሆኗል።

Previous Story

ሞረሽ ወገኔ “ዘረኝነት በቤተ-ዕምነት” የሚል ጽሁፍ በተነ

Next Story

ሳሙኤል ኤቶ የአፍሪካን እግር ኳስ ለመቀየር እየሠራ ነው

Go toTop