አድዋ ተናገር !! ( አሥራደው ከፈረንሳይ )

February 23, 2023

እምቢኝ ለማተቤ – እምቢኝ ላገር ብሎ ፤
ሚስትና ልጆቹን – እርግፍ አርጎ ጥሎ፤
እርሻው አይታረስ! – አረም ይብላው ብሎ፤
አረም እንዳይበቅል – ባድዋ ተራራ፤
በጎራዴው አርሶ – ጥይቱን የዘራ፤
ጭንቅላት የቀላው – በጩቤ በካራ፤
ድሉን ያደመቀው – በጀግና ፉከራ፤
አልነበረም እንዴ – መላው ድፍን ሃገር?
አድዋ ተናገር!!
በማተብህ ጽና_ ለህሊናህ እደር፡፡

ከሰሜን ከደቡብ – ርቀት ሳይገድበው፤
ከምዕራብ ከምስራቅ – ጠሃዩ ሳይገታው፤
ሆ! ብሎ የወጣው – ላንተ የሞተልህ፤
ሞቱን ባንተ ሽሮ – ድል ያጎናፀፈህ፤
አልነበረም እንዴ መላው ድፍን አገር ?!
አድዋ ተናገር!!
ቃልኪዳን አትፋቅ ማ’ተብ አትበጥስ፤
በደም የተጣፈ ታሪክ አትከልስ፡፡

አድዋ ተናገር! – ማነው የሞተልህ?
ማንስ አስደፍሮ – ማንስ ዘብ ቆመልህ?
ስጋውን አጥንቱን – ማን ከሰከሰልህ?
ሞቱን ባንተ ሽሮ ድል አጎናፀፈህ?!
አድዋ ተናገር – ምንድነው ዝምታው?
ድንበር ያስከበረው – ደሙን ያፈሰሰው?
አንድ ጎሣ ነበር – ላንተ ሲል የሞተው?
ወይስ መላው ሃገር?!
ሲዳሞና_ ሐረር፤
ወለጋና_ ጎንደር፤
ሸዋና_ ወሎየው፤
አሩሲው_ ጎጃሜው፤
ኢሉባቦር_ ከፋው፤
ባሌ_ ጋሞጎፋው
ኤርትራና_ ትግሬው፤
አልነበረም እንዴ – ላንተ ሲል የሞተው?!
በዘር ሳይታጠር – ሃይማኖት ሳይፈታው፣
ጥቅም ሳይደልለው- ድህነት ሳይረታው፡፡

አሁን ዘመን ከፍቶ – አገር ተበትኖ፤
በዘር በሃይማኖት – ጎሣ ተሸንሽኖ፤
አገር እበት ወልዳ – ትል ደሟን ሲጠባ፤
በባንዳ ታጅቦ – ጠላት ቤት ሲገባ፤
አድዋ የኛ ነው! – ላንተ ምንህም ነው!
ይሉን ጀምረዋል – ጥንቱን እያወቅነው፤
አድዋ ያለ እናቱ፤
አድዋ ያለ ኢትዮጵያ የሙት ልጅ ባንዳ ነው፡፡

አድዋ ተናገር!!
ቃልኪዳን አትፋቅ – ማ’ተብ አትበጥስ፤
በደም የተጣፈ – ታሪክ አትከልስ፤
ኧረ ለመሆኑ – ማነው የሞተልህ?!!
ማነው የቆሰለው – ማነው የደማልህ?
አጥንቱን ከስክሶ – ድል ያጎናፀፈህ?!

ቼ!! ብሎ በመትመም – ነጋሪት የመታው፤
አንቢልታውን ነፍቶ – ፎክሮ የወጣው፤
ጎራዴውን መዞ – ጦሩን የሰበቀው፤
አንተ እንዳትደፈር – ቃል ኪዳን የገባው፤
ላንተ የሞተልህ – ላንተ የተሰዋው፣
መላው ኢትዮጵያዊ – ድፍን ሃገሩ ነው?
ወይስ አንድ ጎሣ – ብቻውን ትግሬ ነው??

አድዋ ተናገር!!
ቃልኪዳን አትፋቅ – ማ’ተብ አትበጥስ፤
በደም የተጣፈ – ታሪክ አትከልስ፤
ኧረ ለመሆኑ – ማነው የሞተልህ?!!
ማነው የቆሰለው – ማነው የደማልህ?
አጥንቱን ከስክሶ – ድል ያጎናፀፈህ?!

በህይወቴ እያለሁ – ጠላት አይደፍርህም፤
ጣሊያን ባንተ ጉያ – አይውልም አያድርም፤
ፋሺስት ባንተ መንደር – አይምነሸነሽም፤
ብሎ የተመመው – ላንተ ሊሞትልህ፤
ላንተ የቆሰለው – ላንተ የደማልህ፤
አርነት ያወጀው – ድል ያጎናጸፈህ፤
ኧረ ለመሆኑ – አንድ ጎሣ ነበር ?!
ወይንስ ጦብያ መላው ድፍን አገር ::

አድዋ ተናገር!
በቃል ኪዳና ጽና – ለማ’ተብህ እደር፤
በደም የተጣፈ – ታሪክ አትሸርሽር፤
እንዲህ እንደዛሬው !
ጥላቻን አንግቦ – በዘር ሳይታጠር፤
ላንተ የሞተልህ – መላው ጦቢያ ነበር::

አንድ ቀን

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

የአማራ ምሁራን የመጥፋት ሴራ የተሸረበበትን ሕዝባቸውን እያነቁና እያደራጁ ወይስ አማራ ባዶ “(Amara Frie)” ኢትዮጵያን እየጠበቁ?

Next Story

መግለጫውን የሚመጥን ዝግጅት ተደርጓል ወይ? አብይ ብቻውን ጦርነት አይገጥምም! – አሰፋ በድሉ

Go toTop