በመንግስት አካላት እየተደገፉ በኦሮሚያ ልዩ ዞን ሲሰለጥኑ ከርመዋል የተባሉ አሸባሪ የኦነግ እና የትሕነግ ኃይሎች በኤፍራታ እና ግድም ወረዳ በሁለት ቀበሌዎች ላይ የተደራጀ የወረራ ጥቃት ከፍተዋል፤ በርካታ አማራዎች ሲገደሉ 4 መንደሮች ሙሉ በሙሉ ወድመዋል ሲሉ ነዋሪዎች ተናገሩ።
አሻራ ሚዲያ
ሀምሌ 4 ቀን 2014 ዓ.ም
(© አማራ ሚዲያ ማዕከል/አሚማ)
በኤፍራታ እና ግድም ወረዳ አጣዬ ዙሪያ ከኦሮሚያ ልዩ ዞን የመንግስት አካላት ድጋፍ ይደረግላቸዋል የተባሉ የኦነግ እና የትሕነግ አሸባሪ ቡድን አባላት በሁለት ቀበሌዎች ላይ ወረራ በመፈጸም በርካታ አማራዎችን በመግደል ከ4 በላይ መንደሮችን አቃጥለዋል፤ ወረራቸውን አጠናክረው ቀጥለውበታል ተብሏል።
በኦሮሞ ብሄረሰብ ልዩ ዞን በበጤ ፈጫ ቀበሌ ብቻ 38 የሚሆኑ የትሕነግ የሽብር ቡድን አባላት ጽንፈኛ እና ተስፋፊ ኦነጋዊያንን እያሰለጠኑ ነው በሚል መረጃው ከዞን እስከ ክልል የደረሰ ቢሆንም ጀሮ ሰጥቶ ያዳመጠው እንደሌለ ከጥቃት የተረፉት ይናገራሉ።
“በአስቸኳይ ድረሱልን!” በሚል ጥሪ እያቀረቡ ያሉ ነዋሪዎች እንደገለጹት የተቀናጀ እና የቡድን መሳሪያ የታጠቀ ወራሪ ኃይል ሀምሌ 3/2014 ለመጨፍጨፍ የያዘውን እቅድ ለማስቀጠል በመጀመሪያ በአርሶ አምባ ማኛ ቀበሌ በገበሬዎች አዝመራ ላይ ከብቶችን በመልቀቅ ማሳቸውን አስበልቷል።
ከብቶችን ለማባረር ሲሯሯጡ በነበሩ ገበሬዎች ላይ ጦርነቱን በማስጀመር በዙሪያው ለወረራ አዘጋጅቶት ሲያሰለጥነው የከረመውን የኦነግ እና የትሕነግ ኃይል ከበጤ በኩል እያመላለሰ በማስገባት ሀምሌ 3/2014 ከቀኑ 6 ሰዓት ጀምሮ ከፍተኛ ተኩስ ከፍቶ ውሎ አድሯል።
በዚህም አማራ ሚዲያ ማዕከል (አሚማ) ያነጋገራቸው የአርሶ አምባ ማኛ ቀበሌ አስተዳዳሪ አቶ ማሞ ማስረሻ እንዳረጋገጡት የተቀናጀው እና መንግስታዊ ድጋፍ ያለው የአካባቢው አርሶ አደሮችን በማካተት ወራሪው ቡድን ዋጌና እና በርሃ የተባሉ ሁለት ጎጦችን በማቃጠል ተቆጣጥሯል።
እስካሁን ባለው መረጃ በአርሶ አምባ ማኛ ቀበሌ ብቻ 7 ሰው ተገድሏል፤ 9 ሰዎች ቆስለዋል፤ ከ150 በላይ ቤቶች ተቃጥለዋል፤ ከ176 በላይ ገበሬዎችን የቀንድ ከብቶች እና የጋማ ከብቶችን በቀላል ግምት ከ10 ሚሊዮን በላይ ንብረት ተዘርፏል።
በስናይፐር እና በብሬን የጀመሩት ግልጽ የወረራ ጦርነቱ ቀጥሏል የሚሉት አቶ ማሞ ሀምሌ 4/2014 ከጠዋቱ ጀምሮ ከአርሶ አምባ ማኛ ቀበሌ በተጨማሪ በመንተኬ ሸረፋ ቀበሌ ላይም ከጠዋቱ 1 ሰዓት ጀምሮ ሙሉቀን ሲወሩ እና ሲጨፈጭፉ ውለዋል።
በቀጠለው ግልጽ ወረራ እስካሁን ከተቃጠሉ መንደሮች መካከል:_
1) ከአርሶ አምባ ማኛ ቀበሌ:_
ሀ) ዋጌና እና
ለ) በርሃ የተባሉት ሰፈሮች እንዲሁም
2) ከመንተኬ ሸረፋ ቀበሌም:_
ሀ) ስረጌ፣
ለ) መዲና እና
ሌሎች መንደሮች ይገኙበታል።
በመንተኬ ሸረፋ ቀበሌ ጂሌ አምባ፣ሼህ ኡስማን እና ጃለሌ በሚባሉ መንደሮችም ቃጠሎ እንዳለ
ተነግሯል።
የመንተኬ ሸረፋ ቀበሌ ዋና ከተማን ብርቂቶን ለመቆጣጠር በቅርብ ርቀት ያሉትን ስረጌ እና መዲናን አቃጥለው እየቀጠሉ ይገኛሉ ተብሏል።
ሀምሌ 4/2014 ከረፋዱ 4 ሰዓት ላይ አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ቀይ ባንዴራ ይዘው ከፌደራል ለማረጋጋት ነው የመጣን በሚል በመኪና የገባው ተጨማሪ ኃይል ነዋሪዎችና ልዩ ኃይሉን በማዘናጋት ነው ጭፍጨፋውን የፈጸመው።
ሀምሌ 3/2014 ምሽት ገብቶ ከነበረው የአማራ ልዩ ኃይልም በርካቶች መገደላቸውን የአሚማ ምንጮች እየተናገሩ ነው።
አንድ የዐይን እማኝ ሁለት ልዩ ኃይሎች ተመተው ሲወድቁ እና መሳሪያቸውን ገፈው ሲወስዱባቸው ተመልክቻለሁ ብለዋል።
የሰሜን ሸዋ ዞንም ሆነ የአማራ ክልል መንግስት በከሚሴ እና በአካባቢው ማን የት ላይ እንደሚሰለጥን፣ የያዘውን ትጥቅ ጭምር እያወቀ በዝምታ ከመመልከቱም በላይ ለሁለት ቀናት ያህል ግልጽ ወረራ እና ጦርነት ሲከፈትበት ተጨማሪ ኃይል ለማስገባት አለመድፈሩ በእጅጉ እንዳሳዘናቸውና ከነገሩ እጁ እንዳለበት ያመለክታል ብለዋል።
ዘገባው የአማራ ሚዲያ ሴንተር ነው።