ማተቡን ከቆረጠ (ዘ-ጌርሣም)

May 15, 2021

ክሯን ሳይሆን
ቃሉንና የማይታየውን
በድምፅ የማይሰማውን
በእጅ የማይዳሰስውን
ህሊና ብቻ የሚያውቀውን
ለሰው ልጅ የተሰጠውን
ግዑዙን ቃል ነው
ማተብ መታመን ነው የምንለው
ማንም ማተቡን ከቆረጠ
ከሃዲነቱን በአደባባይ ከገለጠ
በራሱ ባልሆነ ለመክበር ቋምጦ
ሰብዕናውን ለነዋይ ሽጦ
ደፋ ቀና ከሚል
ቢያውቅ መልካም ነበር ቢያስተውል
ይህን መረዳት አቅቶት በጥፋቱ ከቀጠለ
አይሻልም ከቆሻሻ ከተጣለ
ሁለንተናውም ይሟጠጣል
ከአራዊት ዘር ይመደባል
የሰው ልጅ ክቡር መሆኑ ተረስቶ
በጊዜ ዋቢነት ተዳኝቶ
እርቃኑን ይቀራል ተራቁቶ
ድሮ በደጋጎቹ ዘመን
ሰው ይረከብ ነበር አደራን
በሕይወት እስካለ የድርሻውን
ምላሱን ላያጥፍ ላይከዳ ህሊናውን
ያኔ ማተብ ሲባል
ፊርማ ሳይኖረው በቃል
የአብሮነት ህግ ነበር
እምነትን በቃል የሚያስከብር
ቃል በሰማይ ቃል በምድር አስብሎ
ማተቡን በልብ ዳኝነት አስምሎ
ይረከብ ነበር አደራውን
በሕይወት እስካለ የድርሻውን
አይቀሬው ሞት እንኳን ሲመጣ
ቃሉን ለማጠፍ ሳይቃጣ
ያወርስ ነበር አደራውን
በቃል የተረከበውን
ለባለቤቱ እንዲያስረክብ
እምነት በቃሏ እንድታብብ
አደራ ተረካቢም በበኩሉ
ይታመን ነበር ለቃሉ
ቃል እምነት መሆኗን
ይረዳ ነበር ሐቁን
በዚህ መልኩ ትውልድ ይቀጥል ነበር
ዛሬ እንዲህ ላይኖር
ተረት ተረት ሆኖ ሊቀር
ማንም ማተቡን ከቆረጠ
ከሃዲነቱን ከገለጠ
በራሱ ባልሆነ ቋምጦ
ሰብዕናውን ለነዋይ ሽጦ
ደፋ ቀና ከሚል
ይነገረው እንዲያስተውል
መታመንን ቃሌ ነው ይበል
ትውልድም በሕግጋቱ ይቀጥል

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

ሚዲያ ይዘጋ የሚል ካድሬ እንጂ ጋዜጤኛ አይደለም- የኢትዮጵያ አገር አድን ግብረኃይል

Next Story

በአስከፊ ሁኔታ እራሱን እየደገመ የቀጠለው የፈሪዎችና የጨካኞች የፖለቲካ ሴራ – ጠገናው ጎሹ

Go toTop