የአዲስ አበባ የባቡር ሐዲድ በውሉ መሠረት ባለመነጠፉ እየተቀየረ መሆኑን ኮርፖሬሽኑ አስታወቀ

June 15, 2014

በአዲስ አበባ ከተማ ቀላል የባቡር መስመር ላይ ቀደም ብሎ የተነጠፈው ሐዲድ ከውሉ ውጪ የተከናወነ በመሆኑ በመቀየር ላይ እንደሚገኝ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡

በምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የአዲስ አበባ ከተማ የባቡር ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር በኃይሉ ስንታየሁ ባለፈው ዓርብ በፕሮጀክቱ አካባቢ ለጋዜጠኞች በሰጡት ማብራርያ፣ የቻይናው ኩባንያ በኮንትራት ውሉ መሠረት ሐዲዱን እንዲያነጥፍ በኮርፖሬሽኑ አማካሪ ድርጅት በመታዘዙ በመቀየር ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ቀደም ብለው የተዘረጉት ሐዲዶች እርስ በእርስ የተያያዙት በብሎን መሆኑን ያስታወሱት ሥራ አስኪያጁ፣ ‹‹የኮንትራት ስምምነቱ ግን በኃይድሮጅን ብየዳ መከናወን እንደሚገባው ይገልጻል፤›› ብለዋል፡፡

በብየዳ እንዲያያዙ መደረጉ ‹‹ከጥንካሬ፣ ከደኅንነትና ከምቾት አንፃር ጥቅም ስላለው ነው›› የሚሉት ኢንጂነር በኃይሉ፣ በሚነሱትና በሚቀየሩት ሐዲዶች መካከል የምርት እንጂ የጥራት ልዩነት የለም ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት እየተከናወነ ያለው ሐዲዱን የመቀየርና የመበየድ ሥራ እንጂ ‹‹ሐዲዱ የሚያርፍበትን ርብራቦችና ባላንስ ጠጠሩን የማንጠፍ አይደለም፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

‹‹ከቻይናው ኩባንያ ጋር የተፈረመው ስምምነት የኢንጂነሪንግ፣ የግዥና የግንባታ ሥራዎችን አጠናቆ የፕሮጀክቱን ቁልፍ የማስረከብ ኃላፊነት በመሆኑ፣ በዚህ ሐዲድ የመቀየር ሥራ በራሱ ጊዜና የገንዘብ ወጪ የሚሸፈን ነው፤›› ብለዋል፡፡

እስካሁን ድረስ ኮንትራክተሩ ያቀረበው የጊዜም ሆነ የወጪ ኪሳራ አለመኖሩን የተናገሩት ሥራ አስኪያጁ፣ ቢያቀርብም ከውሉ ውጪ በመሥራቱ የመጣ በመሆኑ አማካሪ ድርጅቱ አያፀድቅለትም ብለዋል፡፡

ሐዲዱን የመቀየር ሥራ እየተከናወነ ያለው ሐዲዱ ቀድሞ በተነጠፈባቸው ቦታዎች በሙሉ መሆኑን ኢንጂነር በኃይሉ አስረድተዋል፡፡

Source: Ethiopian Reporter

Previous Story

ሱዳን ሃገር የሚገኙ የኢትዮጵያውያን ስደተኞች ጉዳይን የሚዳሥስ አራተኛ ፁሁፍ (ካርቱም ሱዳን)

Next Story

ፍርድ ቤቱ ግቢ ውስጥ ከጠበቃ አምሐ ጋር የተደረገ ቃለ ምልልስ

Go toTop