ከምዕራብ ሸዋ ተፈናቅለው በፌዴሬሽኑ አፈ ጉባዔ አግባቢነት የተመለሱት ዜጎች መሬታቸውን በሃይል ተነጠቁ

April 9, 2014

ከዳዊት ሰለሞን

ከሰላሳ የማያንሱ የምዕራብ ሸዋ ዞን አምቦ ዳኖ ወረዳ ባጅላ ዳሌ ቀበሌ ገ/ማህበር ነዋሪዎች ‹‹ ወደ ክልላችሁ ተመለሱ ›› ተብለው መሬታቸውን ለመነጠቅ መቃረባቸውን ለማመልከት አዲስ አበባ በመምጣት የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ካሳ ተ/ብርሃንን ካናገሩ በኋላ አፈ ጉባኤው ‹‹ወደ ቀዬአችሁ ተመለሱ እኔ ችግሩ እንዲፈታላችሁ አደርጋለሁ››በማለታቸው ገበሬዎቹ ወደ አምቦ መመለሳቸው አይዘነጋም፡፡

ወደ አምቦ የተመለሱትን ገበሬዎች የዞኑ ሃላፊዎችና የኦህዴድ ካድሬዎች ‹‹አዲስ አበባ በመሄድ ገመናችንን አጋለጣችሁ››በማለት ሲዝቱባቸው መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ከትናንት ጀምሮም የታጠቁ ሚሊሻዎችን በማስከተል የቀበሌ ገ/ማህበሩ አመራሮች‹‹መሬታችንን ለቃችሁ ወደ መጣችሁበት ክልል ተመለሱ ››በማለታቸውና ገበሬዎቹ ‹‹ አንለቅም ከዚህ ውጪ አገር የለንም›› ቢሉም በመሳሪያ በማስፈራራት ከአካባቢው እንዲርቁ በማድረግ መሬቱን ለሚፈልጓቸው ሰዎች ማከፋፈላቸውንና ሊደበድቡንና ሊገድሉን ይችላሉ ብለው የሰጉ ገበሬዎችም ልጆቻቸውንና ባለቤቶቻቸውን በመያዝ ጫካ መደበቃቸውን በስልክ ከስፍራው ያናገርኳቸው ሰዎች ገልጸዋል፡፡ገበሬዎቹ ከዛሬ ሀያ ዓመት በፊት ከጎንደር አካባቢ ተፈናቅለው አሁን ለስደት በተዳረጉበት አካባቢ የሰፈሩ ነበሩ፡፡

ገበሬዎቹ ለአቤቱታ አዲስ አበባ መጥተው በነበረበት ወቅት ለምን አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ጋር ሄዳችሁ ተብለው መታሰራቸው አይዘነጋም፡፡

Previous Story

የኦሮሚያ ልዩ ዞኖችን በሚያጠቃልለው ማስተር ፕላን ላይ መግባባት አልተቻለም

Next Story

ነገረ ኢትዮጵያ ቁጥር 7

Go toTop