የምንመርጠው የህይወት  መንገድ እና ጥምረት  የነጋችን መሠረት ነው ።

February 19, 2025

መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

“If you cannot find a good companion to walk with, walk alone, like an elephant roaming the jungle. It is better to be alone than to be with those who will hinder your progress . “

Gautama Buddha

“  የዓለማህ ተባባሪ   ወይም አቻ የሆነ ጥሩ ተጣማሪ ተጓዥ ካላገኘህ ፣ ብቻህን   መጓዝ ምረጥ  ። ልክ ጫካውን እያተረማመሰ ወደ ግቡ እንደሚጓዝ ዝሆን ። ከጉዞህ ከሚያደናቅፍህ ጓደኛ ይልቅ ዝሆናዊ ጉዞን ብትመርጥ ይበጅሃል ። “ የጥቅሱ መጨረሻ ።

ከዚህ ጥቅስ የምንማረው ፣ በህይወት መንገድ ላይ አስተዋይ ፣ ብልህና ጥበበኛ ሰው የሚያጋጥመውን መሰናክል በስኬት ማጠናቀቅ ወይም መሰናክሉን ማለፍ የሚችለው ከብልህ ባልንጀራ ጋር በመሆን ፣ የሚያጋጥመውን ችግር በእኩል ስሜት ና በአንድ ልብ ሆኖ በማሸነፍ  በመጓዝ  እንጂ ከራዕይ አልባ ጓደኛ ጋር ያለ ዓላማ በደመነፍስ በመጎዝ እንዳልሆነ ነው   ።

ሁሉንም የህይወት ፈተናዎቾ በየፈርጁ በመፈተሽ በዘዴ ና   በመላ በድል ለመወጣት የሚቻለው በህይወት መንገድ  ዓላማ ካለው ሰው ጋር ሲጣመሩ እንጂ በደመነፍስ በመጓዝ አይደለም ። በደመነፍስ ፣ በዘፈቀደ እና በምንግዴ በጣምራ  መጓዝ  ለውድቀት  ይዳርጋል ።

ሰው ሁሉ በህይወት ዘመኑ መጀመሪያ የሚመርጠው ጓደኛ ደመነፍሳዊ የህይወት ጉዟን አራማጅ ከሆነ አጥፊው  ይሆናል ። እናም ነፍስ አውቆ ብቻውን በህይወት ጎዳና መጓዝ ሲጀምር መልካም  ቅን ፣ አርቆ አሳቢ ፣ ሃይማኖተኛ እና ከማንኛውም ሱስ የፀዳ ጎደኛ ካለ መረጠ ወይም ብቻውን በንፁህ ህሊና ፈጣሪ በመረጠለት ጎዳና መጓዝ ካልጀመረ በስተቀር ከድሉ ይልቅ ሽንፈቱ ፤ ከስኬቱ ይልቅ ውድቀቱ የጎላ ይሆናል ።

ሰው በህይወት መንገድ ሲጎዝ በተለያየ ምክንያት ውድቀት ቢያጋጥመውም ትልቁ የውድቀት ሰበብ ወይም ምክንያት የሚከሰተው  ፣ በፍፁም ቁርጠኝነት ኑሮውን ለመለወጥ በትክክለኛው መንገድ ሲጎዝ ሣለ  ፣ በመንገዱ  ሞኝ ፣ ጅልና ጅላፎ ሰው  ፣ አብሮት እንዲጎዝ ሲፈቅድ ነው ።

ለህይወት ግድ የሌላቸው እና ለገዛ ነፍስያቸው የማይጠነቀቁ ሰዎች በደመነፈስ የሚኖሩ  ህልም አልባ በመሆናቸው  “ ከአህያ ጋር የዋለች በቅሎ …ተምራ እንደምትመጣ “ ሁሉ መጥፎ ምግባርን አለማምደው ለውድቀት ሊዳርጉን ይችላሉ ። እናም በእነዚህ ራዕይ አልባ ሰዎች ሰበብ ፣ ቀና ልብን ይዞ በህይወት ጓዳና የሚያጋጥመውን ሁሉ በትግል ለመወጣት ቆርጦ የተነሳ ሰው ፣ ጠማማ ባህሪን ይወርስና  በህይወት እና በኑሮው ተስፋ የመቁረጥ ባህሪን ቀስ በቀስ በማዳበር ሙሉ ለሙሉ ከሥኬት ጎዳና ወጥቶ በውድቀት ጎዳና ላይ ሊታይ ይችላል ።

የማንኛውም ሰው ቀና ልቦና አንዴ  ከተጣመመ ፣ ድርጊቱ ሁሉ ከሞራል ውጪ ይሆናል ። ሰው ሁሉ በሂደት ነው ሞራል አልባ እና ህሊና ቢስ የሚሆነው ።   እየተጣመመ የሚመጣው  ። በመንገዱ ላይ ከሚያገኛቸው ፣ ከቤተሰቡ ፣ ከጎረቤቱ ፣ ከማህበረሰቡ ፣ ከትምህርት ቤት እና ከማህበራዊ መድረኮች  ፣ ወዘተ ።  መጥፎ ምግባርን በመቅሰም  ። …

ዛሬ ደግሞ መጥፎ ምግባርን መዳፋችንን በምታክለው የሞባይል ሥልክ ለመማር በምንችልበት ዘመን ላይ ደርሰናል ። በዚህ ዘመናዊ “ በየነ መረብ “ በመጠቀም ቅን ፣ በጎ፣ ታታሪ ፣ ጥበበኛ ፣  ወዘተ ። የሆኑ መኖራቸው እርግጥ ቢሆንም ፤ በተገላቢጦሹ   ህሊናቸውን  እና ጤናቸውን ያጡ ብዙ ሰዎች አሉ  ። ሌላ ፣ ሌላውን ትተን በየነ መረብ የሚስተናገደው ፣ የቴሌግራሙ እና የቲክቶክ ቻናል  ትውልዱ ካልባነነ እና መርጦ ካልተከታተለው በፍጥነት  ወደ ሞት እና ወደ ውድቀት እንደሚያደርሰው እየታየ ነው  ።

ዘመን እና  ጊዜ ሁሉንም ነገር በበየነ መረብ በኩል እካችሁ ብሎናል ። ዕውቀትን በሙሉ በቲዎሪና በተግባር ከበየነ መረብ ማግኘት ተችሏል ። ተራ ወሬን ጨምሮ አገር ነቅናቂ ዜና በደቂቃዎች ውስጥ በሁሉም ዓለም ይዳርሳል ።  የሚያነቃቁ ፣ የሚያዝናኑ ፣ የሚያስተምሩ እንዲሁም ሥድ የሚያደርጉ ቪዲዮዎችን እያማረጡ ከተለያዩ ዩቲበሮች በፈለጉት ሰዓት ማግኘት ተችሏል ።

ይኽ እውነት የሚያመለክተን ፣ የዛሬው  ትውልድ ዕውቀትን የማግኘት ችግሩ በኢንተርኔት አማካይነት  እንደተቃለለለት ነው ። በዚህ በጎ ተፅዕኖ የተነሳም ፣ ብልህ እና ቅን ልብ ያለው ወጣት ከሚያስተምረው አስተማሪ  የበለጠ እውቀት ይዞ ክፍል ውስጥ በመገኘት መምህሩን ሊሞግተው ወይም እውቀቱን ሊያዳብርለት ይችላል  ። በዚህ ረገድ ለወጣቱ ኢንተርኔት ወንዝ አሻጋሪ የዕውቀት  ጓደኛው ለመሆን  ችሏል ።

በተቃራኒው ደግሞ ጎታች ና ወደ  አዘቅት ጣይ ዌብ ሳይቶች በሽ ፣ በሽ ናቸው ። በዚህ የሞት መንገድም በመጎዝ    በገዛ እራሱ የራሱን የመቀበሪያ ጉድጎድ  ቆፍሮ    በቁም የተቀበረ    ጥቂት አይደለም  ።  ስለዚህም ነው ” ከጅምሩ ቀና እና አሻጋሪ የህይወት ጎደኛ በኮበሌነትህ ምረጥ አልያም በራስህ ቅን ልቦና በእምነትህ ፀንተህ ብቻህን በመንገድህ ተጉዘህ ስኬትህን እውን አድርግ ። ”  ብለን ለመመከር በዚህ ጽሑፍ የተነሳነው ።

ማንኛውም ቅን እና የዋህ ሰው ባለመው የስኬት ጎዳና ሲጎዝ  በጎና ቅን  ህሊና ያለው ሰው በመንገዱ ካልተቀላቀለው እና ከህልም አልባ ፣ ምንግዴ  ሰው ጋር ጉዞ ከጀመረ   ያሰበው ስኬት ላይ ለመድረስ ከቶም አይችልም ።  ምናልባትም ያሰበው የስኬት ጉዞ ሊሰናከል  ወይም ሩቅ አስቦ ቅርብ ሊያድር ይችላል ።

እንኳን የህይወት ጉዞን ይቅርና ተራ የመንገድ ጉዞን እንኳን ከጅል ሰው ጋር መጓዝ   ፣ ጉዞውን  እጅግ አሰልቺ  ያደርገዋል ።  ወይም አጭሩ መንገድ እጅግ ይረዝምበታል  ።  መንገዱ ጨርቅ አይሆንለትም ። ለዚህም ነው ጉተማ ” ከጅል ጋር ከመጓዝ ለብቻ መጎዝ ይመረጣል  ። ” በማለት አጥብቆ  የመከረው ።

የጉተማ ቡዳኸ መልዕክት ፣ በህይወትህ አጭር ጉዞ ወቅት ፣   በአንተ መንገድ ላይ የሚጓዘውን የበዛ ሰው በጥያቄዎች በመርምር እና እውቀቱ የመጠቀ ወይም የኮሰመነ መሆኑንን በመረዳት ጉዞህን አንድ ላይ ለማድረግ መወሰን ብልህነት ነው ። ዋናው  ጥያቄ ”  አብሮህ ለመጎዝ የተነሳው ሰው ማነው ነው ? ” በቅድሚያ  ማንነቱን ማወቅ አለብህ ። እንከፍና ጅላንፎ ከሆነ ፣ የእርሱን የጉዞ አቅጣጫ ጠይቀህ በመረዳት  ፣ የአንተን የጉዞ አቅጣጫ ከእርሱ በተቃራኒ እንደሆነ በማሳወቅ ከጉዞህ አቅጣጫህ  ጅሉን ሰው ማራቅ ይገባሃል ። አልያም መንገድህ ሳያልቅ ” ጉዞዬን አጠናቀቅሁ ። ይኸው በቃ ደረስኩ  ። ጉዞዬ ተጠናቀቀ ። ” ብለህ  በዘዴ በጊዜ መለየት ከመሰናከል ያድንሃል  ። ይሁን እንጂ አብሮ ለመያዝ  የተቀላቀለህ ሰው ፣ ከአንተ በላይ ብልህ ሊሆን ስለሚችል ፣ ማንነቱን ለመረዳት  በጥበብ የተሞሉ የህይወት ጥያቄዎችን ጠይቀው ።

ስለ ህይወት እና ሞት ፤ ሰለ ሥራ እና ሥንፍና ፤ ስለተድላና ምንዱባንነት አንስተህ ሃሳቡን ተረዳ ።  ለአፍታ ብልህ ነው ወይስ ብልጣብልጥ ብለህ ፣ በህሊናህ   ገምግመው ። ጥያቄህን በወጉ ከመለስ አብረኸው ተጎዝ ። እርሱ ተጨማሪ የህይወት ትምህርትን ያጎናፅፍሃልና ።  ካልመለሰ ደግሞ በዘዴ ተለየውና  ብቻህን ተጎዝ ።

ብቻህን በመጓዝህ  እምብዛም አትጨነቅ ። በመጀመሪያ ነገር ማወቅ ያለብህ እያንዳንዳችን ወደ ምድር የመጣነው  ብቻኛ ሆነን  ነው ። ከእኛ ጋር የተጣመረ ሌላ ሰው የለም ። የመጣነው ብቻችንን ነው ። ምድሪቶን የምሰሰናበታትም  ለየብቻ ነው ።  በተራ ፣ በተራ እንቀባበራለን ። ተራ ሟቾች ለሞች እየለቀስን  ።

ከአንድ መሐፀን በደቂቃዎች ልዩነት ብንወጣ እንኳን  በደቂቃዎች ልዩነት  በአንድ ቀን  አንሞትም ። በአንድ ቀን እና በእኩል ሰዓት የመሞት አጋጣሚ ከሚሊዮን አንድ ሊሆን ይችላል  ። …እናም ሰዎች  ሁሉ ህልውናችን ለየብቻ ነው ። በጣምራ አይደለም ። በግለሰብ ደረጃ ነው ህይወትን የምንኖራት ። ሰዎች በባዮሎጂካል አቋማችን አንድ ግለሰብ መሆናችንን መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው ። ራሱን ፣ ግለሰብነቱን ያልተረዳ  ወይም  በሚገባ ያልተረዳ ከሌላ ጋር ቢደባለቅ  ዜሮ አበርክቶ ነው ያለው  ።

ሰው ግለሰብነቱን በመረዳት የሌሎችን ግለሰቦች ማንነት ለማወቅ በፅሞና ሊመረምራቸው እና ሊያዳምጣቸው ይገባል ። እርግጥ ነው አንድ ግለሰብ ምን ያህል አስተዋይ እንደሆነ ማወቅ የሚቻለው ግለሰቡ እንዲናገር ዕድል በመሥጠት ነው ። መቼም “ ሲቪህን አሳየኝ “ አትሉትም ። እርሱ  የግለሰቡን ስብዕና እና እውቀት በትክክል አይገልፀውም ። …ያውም በእኛ አገር የተዝረከረከ የመማር ማስተማር ሂደት የተለያዩ ዲግሪዎች የባለዲግሪውን እውቀት አይመሰክሩም ። የሰው እውቀቱን ለመመስከር የሚቻለው በተግባሩ ነው ። አብረኸው ስትሰራ ወይም አገልግሎቱን ስትፈልግ ብቃቱን ትረዳለህ ። ያን ጊዜ ታደንቀዋለህ ። ያን ጊዜ ዲግሪውን እንደገዛ ትገነዘባለህ ። ወዳጄ ህይወት ስታስተሳስርህ ነው ሰውን በቅጡ የምታውቀው ።

እኛ ሰዎች ከሌሎች ፍጡራን የምንለየው በማህበራዊ ግንኙነት በመተሳሰራችን  ነው ። ህይወታችን ና ኑሮአችን በማህበራዊ ኑሮ እና በተስማማንበት እና ባልተስማማንበት ህግ የተጋመደ ነው ። ሰው ከሰው ጋር ያለማህበራዊ ግንኙነትና ያለህግ በወጉ መኖር  አይችልም ።

ይኽ ማለት ግን አንድ ላይ ተጣምሮ በአንድ ሥፍራ እንዲኖር ይገደዳል ማለት አይደለም ። ወይም አብሮት የሚኖረውን ለመምረጥ አይችልም ማለት አይደለም ።

አብረህ ለመኖር ኃይማኖትህ ፣ ባህልህ ፣ የአእምሮህ ግዝፈትህ ፣ የምትኖርበት አገር ሥልጣኔ እና መልካምድሩ የጎላ ሚና ይጫወታሉ ።

ምንም እንእንኳኳ በአፈጣጠሩ ሰው ከሌሎች ፍጡራን ቢለይም  ፤  በፍጥረቱ እፁብና ድንቅ ቢሆንም ፣ ከሚኖርበት ህብረተሰብ በኑሮ ሂደት የቀሰመው ገንቢና አፍራሽ ትምህርት ፣ ጠቃሚና ጎጂ ባህል ና ኃይማኖት በአስተሳሰቡና በአመለካከቱ ላይ ተፅኖ ያሳድርበታል  ። …

ሰው ማለት በራሱ ሙሉ የሆነ  የተሟላ ማለት ቢሆንም    ። ነፍሱ እስካልወጣች ጊዜ  ድረስ በራስ ተነሳሽነት ያለአንዳች አሥገዳጅ አጋጣሚ ድንገት በአዲስ ድርጊት ተከስቶ ሊያስገርመን ይችላል ። ነገ ራሳችን ተመሳሳይ ድርጊት ስንፈፅም ደግሞ በተራው እርሱ ይገረማል ።

እንግዲህ ይህ ድንገቴ ድርጊትን ለመቆጣጠርና አውዳሚ እንዳይሆን ለማድረግ ፣ ሰው በተፃፈና ባልተፃፈ ህግ   እንዲመራ ወይም እንዲያድር ተደርጓል  ።

ያም ቢሆን  ሰዎች በእርስ በእርስ ግንኙነት ጊዜ ሰው በመሆናቸው ብቻ ሥለጋራ ችግራቸው በመወያየት ጓደኝነት ሊፈጥሩ ቀስ በቀስም በአስገዳጁ የኑር ሁኔታ ላይ የጋራ መፍትሄ ለማምጣት ሊመክሩ ይችላሉ ። መምከር ብቻ ሳይሆን ድንገት  አንዳች አብዮት እንዲቀጣጠል ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ ።

እርግጥ ነው ፣ ከአምሳያው ጋር ተቀላቅሎ አብዮተኛ ለመሆን የሚችል ሰው እንዳለ ሁሉ ፣   ያለአንዳች ተሳትፎ ራሱን አግልሎ በመቀመጥ በጥልቅ በማሰብ ዓለምን የሚለውጥ ሃሳብ ሊያመነጭ የሚችልም ኃያል አእምሮ ያለው ግለሰብም ይኖራል ።

እንግዲህ ያንን እና ይህንን  አይነቱን  የግለሰብ ስብስብ ነው  ፤ ” እኛ  ” የምንለው ። ህዝብ የግለሰቦች  ስብስብ ነው   ። …

ህዝብ የግለሰብ ስብስብ ነው ። ግለሰብ ማለት የማይካፈል ማለት ነው ። የእንጊሊዘኛውን ” ኢን ዲይቪይጇልን ” ውሰዱት ። ግለሰብ ማለት አንድ ና ያው ማለት ነው ። ነገር ግን ግለሰብች  በውስጣቸው የሚጋጩ አያሌ የህሊና ሙግቶች የሉባቸውም ማለት አይደለም ። ። እናም ጥሩ ሥራቸው ጎልቶ በሰዎች ዘንድ ሲታይ “ የእኔ ቲሩፋት ወይም ግኝት ነው ። “   ብለው ሊኮፈሱ ይችላሉ ። መጥፎ ሲሰሩ ደግሞ “ ሤጣን አሳሳተኝ  ። “ የሚሉ ጥቂቶች አይደሉም ። እጅግ ስኬተማ ሲሆኑ ራሳቸውን ሲያደንቁ እናገኛቸዋለን ። በዝቅታ ደረጃ እና በችግር ውስጥ ሲወድቁ ደግሞ በአርባ ቀን ዕድላቸው ሲያማርሩና በመተት ፣ በድግምት ፣ በጠንቆይ ሥራ ሲያመካኙ እናስተውላለን ።

እውነቱ ግን ይኽ አይደለም ። እውነቱ ነፍስ አውቀው ፣ ለአቅመ አዳምና ሄዋን ደርሰው ፣ በፍላሎታቸው ሰዓት በህይወት መንገድ ላይ ሲጎዙ የመረጡት መንገድ ለዛሬ ታላቅ ሰብዕና አደርሷቸዋል ። አልያም የመረጡት የጥፋት መንገድ ለታላቅ ውድቀት ዳርጓቸዋል ። ጉተማ ቡዳኽ እንዳለውም በፍላሎት ዘመን ከጅል ጋር ተጉዘው እስከወዲያኛው ተጃጅለውም ሊሆን ይችላል ።…

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

የፕሬዚደንት ዶናልድ ትረምፕ እንደሽጉጥ ያነጣጠረና የህግን የበላይነት የሚጥስ ፖለቲካ!

Next Story

እንደገና ሰው እንድንሆን፣ እንደገና አገር እንዲኖረን፣ እንደገና መንግሥት እንዲኖረን …

Go toTop