ሕዝቡ የክልሉ መንግሥት ያቀረበውን የህልውና ዘመቻ ጥሪ ተቀብሎ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን የአማራ ክልል መንግሥት ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ግዛቸው ሙሉነህ አስታወቁ፡፡
አቶ ግዛቸው ሙሉነህ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ የክልሉ መንግሥት ያቀረበውን የክተት ጥሪ ተቀብሎ ማኅበረሰቡ ሀብት ንብረቱ ለዘመቻው እንዲውል ለመስጠት፣ አካባቢውን ነቅቶ ለመጠበቅና ተደራጅቶ ወደ ግንባር ለመትመም ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፡፡
አሁን የተጠራው የክተት ጥሪ ለሦስተኛ ጊዜ የተደረገና የክልሉ ምክር ቤት ያወጣቸው አስገዳጅ ጥሪዎችንም ያካተተ መሆኑን ጠቁመው፤ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች መደበኛ ሥራቸው አቁመው የህልውና ዘመቻውን ሥራ የሚደግፉ ሥራዎችን ብቻ አተኩረው እንዲሠሩ፣ የሥራ ማስኬጃ በጀትም ከዚህ ሥራ ጋር ለተገናኘ አገልግሎት እንዲውል ተወስኗል፡፡
ይህ ማለት መሥሪያ ቤት ይዘጋል ማለት ሳይሆን ሠራተኛው እረፍት መውጣቱንም ትቶ ሁሉም ሠራተኛ በሰዓቱ ገብቶ የሚዘምተው ሠራተኛ እንዲዘምት ፣ ስንቅ የሚያዘጋጀው ስንቅ እንዲያዘጋጅና እንዲያቀብል የፕሮፓጋንዳ ሥራ የሚሠራውም እንዲሠራ በአጠቃላይ የህልውና ዘመቻውን የሚደግፍ ሥራ እንዲሠሩ ይደረጋል ማለት መሆኑን ጠቁመው፤ የትምህርት፣ የጤናና የፍትህ ተቋማት ግን መደበኛ ሥራቸውን እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
****************
(ኢ ፕ ድ)