ሱዳን በኢትዮጵያ ድንበር አካባቢ በወረራ በያዘቻቸው ቦታዎች ላይ ድልድዮችን እና የጦር ሰፈሮችን ለመገንባት የያዘችው እንቅስቃሴ ተቀባይነት የለውም ሲሉ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ አስታወቁ። የአረብ ሊግ በህዳሴው ግድብ ላይ የያዘውን አቋም በድጋሚ እንዲያጤነው አልጀሪያ ጥረት እንደምታደርግ ማስታወቋም ተገልጿል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በሳምንታዊ መግለጫቸው እንዳስታወቁት፤ የሱዳን ጦር በኃይል ወረራ በማካሄድ በያዛቸው የኢትዮጵያ አካባቢ ላይ ድልድዮችንና ወታደራዊ ሰፈሮችን ለመገንባት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ይህ አካሄድ ግን ለማንም የማይበጅ እና ተቀባይነት የሌለው ነው።
ሱዳን በኢትዮጵያ ድንበር አካባቢ ድልድዮችንና ወታደራዊ ሰፈሮችን ለመገንባት እንቅስቃሴ እያደረገች በመሆኑ ከድርጊቷ መቆጠብ አለባት ያሉት ቃል አቀባዩ፤ በድንበር አካባቢው ሱዳን ችግሩን የሚያባብስ ድርጊት መፍጠር እንደሌለባት አስታውቀዋል።
እንደ አምባሳደር ዲና ገለጻ፤ ኢትዮጵያ የድንበሩን ጉዳይ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እያስረዳች ሲሆን፣ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተወካይም በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ ተሰጥቷል። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በምክትል ፀሐፊነት የፖለቲካና የሠላም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ሮዝመሪ ዲካርሎ ከሰሞኑ በኢትዮጵያ ጉብኝት አድርገው በኢትዮጵያ ባለስልጣናት ስለድንበር ጉዳዩ ገለፃ ተደርጓል። በውይይቱ ወቅት ተመድ የኢትዮጵያንና የሱዳንን የድንበር ጉዳይ በቅርበት እንደሚከታተለው ተገልጿል
(ኢ ፕ ድ)