ከጎጃም ኮረንቲ
ሰሊጥ ከጎንደር
ከትግራይ ማሩን
ጨውን ከአፋር፡፡
የፍቅር ሙዚቃ ከወሎ ካሴት
ጥላቻን የሚያርቅ ትዝታ የሚከት፡፡
ከአዶላ ከአሶሳ ከወለጋ ወርቁን
ከሸዋ ወተቱን ቅቤና ስኳሩን፡፡
ሠንጋ ከሐረርጌ
ጋዙን ከሱማሌ
ገብስና ስንዴውን ከአርሲ ከባሌ፡፡
ከኢሉ አባቦራ ከከፋ ቅመሙን
ቡናውን ከጅማ
ከጋምቤላ ሩዙን፡፡
ወደ አርባ ምንጭ ዘልቀሽ
ጨንቻም ጎራ ብለሽ
ዓሣውን፣ አፕሉን ሙዙንም ጨምረሽ
አንች የአገሬ ቆንጆ ነይ በነፍሴ ድረሽ፡፡
አታስቢ ውዴ ቢኖር የተረሳ
አታስቢ ፍቅሬ ቢበዛ የሚያሳሳ
አለልን መርካቶ አለልን ፒያሳ፡፡
ከቶ ምን ይጠፋል ከውቧ አገራችን
ከቶ ምን ይታጣል ከኢትዮጵያ እናታችን
እኛ ከተፋቀርን ካለ አንድነታችን፡፡