በኦሮሚያ ከተሞች ትምህርት መቋረጡ ታወቀ

March 30, 2018

በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ የተለያዩ ከተሞች ውስጥ መደበኛው የመማር ማስተማር ሂደት መቋረጡን መረጃዎች ጠቆሙ፡፡ በክልሉ ያለው የፖለቲካ አለመረጋጋት አሁንም በቀጠለባቸው ከተሞች ተማሪዎች የትምህርት ገበታቸው ላይ እየተገኙ አይደለም ሲሉ ያመላከቱ መረጃዎች፤ ችግሩን ወደ ቀድሞ ሁኔታው ለመመለስ የተደረገው ጥረት አለመሳካቱንም መረጃዎቹ ያክላሉ፡፡ በሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ እና በአዳማ ዩኒቨርሲቲ መደበኛው የመማር ማስተማር ሂደት መስተጓጎሉ የታወቀ ሲሆን፤ በተለይ በሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ሙሉ በመሉ ተቋርጧል የሚያስብል ሁኔታ እንደተፈጠረ ተነግሯል፡፡ በሀሮማያ ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ከተቋረጠ ትንሽ ቆየት ማለቱን እና ተማሪዎቹን ወደ ትምህርት ገበታቸው ለመመለስ በመንግስት አመራሮች እየተደረገ ያለው ውትወታ ሊሳካ አልቻለም ይላሉ ከግቢው የወጡ መረጃዎች፡፡

የዩኒቨርሲቲው አስተዳደርም ሆነ ሌሎች የክልሉ መንግስት አመራሮች ተማሪዎችን በመሰብሰብ የተስተጓጎለው ትምህርት እንዲጀመር ያደረጉት የማግባባት ስራ ከሽፏል ሲሉም ይጠቁማሉ-መረጃዎቹ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በአዳማ ከተማ ከአንደኛ ደረጃ እስከ ከፍተኛ ደረጃ የሚማሩ ተማሪዎች ትምህርት ማቋረጣቸውን የጀርመን ድምጽ ዘግቧል፡፡ ዶይቸ ቬለ የአዳማ ከተማ ነዋሪን አነጋግሮ እንዳሰናዳው ዘገባ ከሆነ፣ በከተማዋ ከአንደኛ እስከ ከፍተኛ ደረጃ ያሉ ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ወደትምህርት ገበታቸው አልተመሰሉም፡፡ ተማሪዎቹ ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ ጥያቄ ቢቀርብላቸውም ትምህርት ለመጀመር ፍላጎት እንደሌላቸው የገለጸው ዘገባው፤ ተማሪዎቹ ያቋረጡትን ትምህርት እንዳይጀምሩ የሚመክር በራሪ ወረቀት በአዳማ ከተማ እየተበተነ እንደሚገኝም ዘገባው ያስረዳል፡፡

ከዚህ ቀደም በኦሮሚያ ሲካሄዱ በነበሩ ህዝባዊ ተቃውሞዎች ወቅት፣ ህዝብ ያነሳቸው ጥያቄዎች ካልተመለሱ በቀር ትግሉ እንደሚቀጥል እና የትግሉ አንድ አካል የሆነው ትምህርት የማቆም አድማም ጸንቶ እንደሚቀጥል ሲገለጽ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ራሱን ኮማንድ ፖስት እያለ የሚጠራው ቡድን በኦሮሚያ ክልል ግድያን ጨምሮ የእስር ዘመቻ በከፈተበት በዚህ ወቅት፤ የዩኒቨርሲቲ፣ የአንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንደማይመለሱ በመግለጽ ላይ ይገኛሉ ሲሉ የመረጃ ምንጮች ያስረዳሉ፡፡ መረጃዎቹ ሀሮማያን እና አዳማን በስም በመጥቀስ ትምህርት እንደተስተጓጎለባቸው ይግለጹ እንጂ፤ በሌሎች የክልሉ ከተሞችም መደበኛው የመማር ማስተማር ሂደት መስተጓጎሉን የሚገልጹ ጥቆማዎች እየወጡ ይገኛሉ፡፡

BBN News March 30, 2018

Previous Story

ፈረስ ተቀይሯል!! ጋላቢው ማን ይሆን? – ጌድዮን በቀለ

Next Story

ምርኮኛ – አገሬ አዲስ

Go toTop