(BBN) ከማክሰኞ ታህሳስ 2 ቀን 2010 ጀምሮ በዝግ ሲካሄድ የቆየው የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ መቋረጡ ተጠቆመ፡፡ ስብሰባው በከፍተኛ ውጥረት ሲካሄድ እንደቆየ በተደጋጋሚ ጊዜ መዘገባችን አይዘነጋም፡፡ የፓርላማ አባላት ‹‹ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ያቀረብነው ወቅታዊ ጥያቄ ምላሽ እስኪሰጥበት ድረስ፣ የፓርላማ ስብሰባዎችን አናካሂድም፡፡›› ማለታቸው ይታወቃል፡፡ በዚህም መሰረት ፓርላማ ተገኝተው በወቅታዊ ጉዳዮች ከፓርላማ አባላቱ ለሚነሱ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲሰጡ የተጠየቁት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የፓርላማ አባላቱን በዝግ አዳራሽ አነጋግረው ነበር፡፡
የፓርላማው አባላት በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ያነሷቸውን ጥያቄዎች፣ የኢህአዴግ ባለስልጣናት እየመከሩበት እንደሚገኙ ተነግሯል፡፡ በዝግ ሲካሄድ የቆየው የድርጅቱ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ የተቋረጠውም፣ የፓርቲው አመራሮች ከፓርላማ አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት መሆኑን መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡ የፓርላማው አባላት በተለይ የኦህዴድ እና ብአዴን ተወካዮች፣ በሀገሪቱ ደም አፋሳሽ ቀውስ የተፈጠረው በምን ምክንያት እንደሆነ፣ ቀውሱን መግታት ያልተቻለውስ ለምን እንደሆነ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ምላሽ እንዲሰጧቸው ጥያቄ አቅርበው እንደነበር ሲነገር ቆይቷል፡፡ የኢህአዴግ አመራሮች፣ ከፓርላማ አባላቱ ለተነሱት ጥያቄዎች ምን ዓይነት ምላሽ እየሰጡ እንደሚገኙ ግን ለጊዜው የታወቀ ነገር የለም፡፡
ዝግ ስብሰባውን አቋርጦ ለፓርላማ አባላቱ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ሌላ ዝግ ስብሰባ ላይ እንደሚገኝ የተነገረለት የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፣ ከተመረጡ የፓርላማ አባላት ጋር እየመከረ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡ ይኸው ዝግ ስብሰባ የተጀመረው ሰኞ ታህሳስ 16 ቀን 2010 መሆኑን የጠቆሙት መረጃዎች፣ ከፓርላማ አባላቱ ጋር እየተደረገ ያለው ዝግ ስብሰባ ዛሬም መቀጠሉን መረጃዎቹ ያክላሉ፡፡ የፓርላማ አባላቱ ለጥያቄዎቻቸው ምላሽ እንዲሰጧቸው በህጉ መሰረት ጥያቄ ያቀረቡት ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ቢሆንም፤ አሁን ግን ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽ እየተሰጠ ያለው ግን በኢህአዴግ አመራሮች መሆኑ ታውቋል፡፡
በሀገሪቱ ለተፈጠሩ ፖለቲካዊ ቀውሶች ተጠያቂው አኔ ነኝ የሚል መግለጫ አውጥቶ የነበረው የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፣ ለተከሰቱት ቀውሶች መፍትኤ አበጃለሁ ብሎ ሲዳክር እንደከረመ ይታወቃል፡፡ ሆኖም፤ ከህዝብ እየቀረበ የሚገኘው ጥያቄ፣ ድርጅቱ ስልጣን እንዲለቅ የሚጠይቅ በመሆኑ፣ ድርጅቱ በቀጣይ ምን መወሰን እንዳለበት እንዳያውቅ እንዳደረገው ምንጮች ይጠቁማሉ፡፡ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አስቀድሞ በጭንቀት እና በውጥረት ውስጥ ሆኖ ሲያካሂድ ለቆየው ስብሰባ መቋጫ ሳያበጅ፣ ስብሰባ አቋርጦ ከፓርላማ አባላቱ ጋር ሌላ ዝግ ስብሰባ መጀመሩ፣ ድርጅቱ የተምታታ መንገድ ውስጥ ስለመግባቱ አመላካች ነው ይላሉ-የፖለቲካ ተንታኞች፡፡