ለዚህ ጽሑፍ መነሻው ሃሳብ ክንፈ ዳኘው በአንድ ስብሰባ ቆሞ የተናገረው አስጸያፊ ንግግር ነው።
ጦርነቱ ትግራይን ወጣት አልባ አድርጓታል የሚባል ተደጋግሞ የሚሰማ ንግግር አለ። ትግራይ ግን ይበልጥ የተጎዳቸው በሽማግሌ እጦት ነው። ሽማግሌ ስንል ያረጀ፣ የሸበተ፣ እድሜው የተጎተተ ሰው ለማለት አይደለም።
ዛሬ በትግራይ እድሜ ጠገቦቹ ሰዎች የመለስ እኩዮች ናቸው። ሕወሃት በትነግ፣ በኢዲዮና በኢሕአፓ በደርግም ውስጥ የነበሩ የዚያን ዘመን የትግራይ ወጣቶችን እስከዘር ማንዘራቸው ደምስሳ ሕውሃታውያን ብቻ በሕይወት እንዲሰነብቱ ማድረጓ ይታወቃል። የሕወሃት መሪዎች ደግሞ ማገዱ እንጂ አልተማገዱም። በሃምሳ አመት ውስጥ በትግራይ በተደረጉት የማያባሩ ስብሰባዎች ኢትዮጵያዊነትን በቀጥታም ሆነ በገደምዳሜ ያንጸባረቁ ሁሉ በወረንጦ ተለቅመው ተወግደዋል። በቤታቸውም ተቀምጠው ከባንዳው ዓላማ በተቃራኒ የሆነ ነገር የተነፈሱም በአንድ ለአምስቱ ጥርነፋ እየተሰለሉ በሚስጥር ተወግደዋል። ቤተክህነቱ ከዋልድባ፣ ደብረ ዓባይ፣ ደብረ ዳሞ ገዳማት ጀምሮ በሕወሃት ታጋዮች ተጥለቅልቆ ዛሬ ሕወሃቶች የትግራይ ተገንጣይ ሲኖዶስ ለማቋቋም እና የኢትዮጵያውንም ሲኖዶስ እንደብልና እንደነቀዝ በልተው ባዶ ለማድረግ ችለዋል።
እና መድረክ ላይ ሽማግሌ መስለው የሚቆሙት እነ ክንፈ ዳኘው፣ ተክለብርሃን (የቁጩ ጄኔራሎች) ወዘተ የሚያቀረሹት ከሽበታቸውና ከእድሚያቸው የሚጠበቅ፣ ትግራይን የሚመጥን ንግግር አለመሆኑ ሊያስደንቀን አይገባም። እድሜያቸው የገፋ አእምሯቸው እዚያው ጉርምስናው ላይ የቀረ የሕወሃት ማደጎዎች ናቸውና። እርጅና እንጂ ሽምግልና አያውቃቸውም።
የኮሌጅ ትምህርቱን አቋርጦ ሕወሃትን የተቀላቀለው ክንፈ ዳኘው ሕወሃት አዲስ አበባ ስትገባ የኮሎኔልነት ማእረግ ተችሮት የጂኔራል ሙሉጌታ ቡሊ ቴክኒካል ኢንስቲቱት ኃላፊ ከተደረገ ጀምሮ ሸዋን (እሱ እንደሚለው) ትርፍራፊውን ሳይሆን ዋናውን ቁርጥምጥም አድርጎ የበላ፣ በመጨረሻም የሕወሃት ጌቶች ተላላኪያቸው አቢይ አህመድን አዘው ወህኒ ያስወረወሩት ሰው ነው።
የአሜሪካ ባለሥልጣናት በመንግሥት ለውጥ ወቅት አንድ የሚፈጽሙት የተለመደ ነውር አለ። እሱም አዲሱ መንግሥት ገና ሥልጣን ላይ እየወጣ ሳለ የሀገሪቱን ወታደራዊና የመሳሪያ ማምረት አቅም ዱቄት ማድረግ ነው። የሶርያ አማጺዎች በድል አድራጊነት ቤተመንግሥት ገብተው እየጨፈሩ ከጀርባ አሜሪካ እንግሊዝና እስራኤል የሶርያን የመከላከያ ተቋማት ቦምብ ሲያደርጉ እንደነበር የዘንድሮ ትዝታ ነው። እኛም ጋር ደርግን እንደጣሉ ወያኔ የኢትዮጵያን የመከላከያ ሠራዊት እንድትበትን፣ የመሳሪያ ክምችት እንድታወድም ከማድረግ አልፈው፣ ወያኔን በበቂ ስላላመኗት ከሕንድ ውቅያኖስ በተተኮሰ ክሩዝ ሚሳይል የበቅሎ ቤቱን የመሣሪያ ዲፖ እስከማቃጠል ደርሰዋል (የፍሥሐ ደስታን መጽሐፍ ያነቧል)። የአየር ኃይልና የባሕር ኃይል አባላትንም ስደትና ፍልሰት በማቀላጠፍ ብዙ ገንዘብ የፈሰሰበትን የጦር ኃይል ባዶ አድርገዋል።
የቄሮን ለውጥ ተከትሎ፣ ክንፈ ዳኘውም ሜቴክ የሚባለው የመከላከያ የመሣሪያ ቴክኖሎጂ ማዳበሪያ ተቋም ኃላፊ ስለነበር ከሕወሃት ሌቦችና ወንጀለኞች ሁሉ እሱ ብቻ ተመርጦ እንዲወገድ እና ተቋሙ በአዲስ ተላላኪ እንዲመራ ተደርጓል። ማስተዋል የተሳነው ክንፈ ደግሞ ከሥራና ዝርፊያ ገበታው የነቀለውን የአልቆቹ አለቃ ዛሬም ባለማወቅ ለማገልገል “ትግራይ ሸዋና ኢትዮጵያን ተሸክማ መኖሯን አቁማ ራሷን የቻለች አገር እንድትሆን የቀደመ ዓላማችንን እናስቀጥላለን” ይላል። የቀደመው ዓላማ የትግራውያን ሳይሆን የእንግሊዞችና የግብረ አበሮቻቸው መሆኑን በዚህ በአዛውንት እድሜው እንኳን ማስተዋል ያልቻለ የሸመገለ ሳይሆን የዛገ ሰው ነው።
በባንዶች ልጆች እጅ ከመውደቋ በፊት ትግራይ ለኢትዮጵያ ባለውለታ ነበረች፣ ኢትዮጵያም (ሸዋም) ለትግራይ ባለውለታ ሆና ነው የኖረችው። ትግራይ በአክሱም አማካኝነት ለኢትዮጵያ የሃይማኖት (አይሁዳዊ፣ ክርስትያናዊ እና እስላማዊ) መሠረት ጥላለች፣ ሸዋም ትግራይ በባእዳን በተወረረች ቁጥር ኢትዮጵያን አስተባብሮ በመዝመት ነጻነቷን አጽንቷል። ከብዙ በጥቂቱ።
ሳይሸመግል የመዛጉ ምልክት ጣልያን ከዓድዋ በፊት በኤርትራና በትግራይ ያስቀጸለውን የሸዋ ጥላቻ ነው ዛሬም ክንፈ ዳኘው የሚያነበንበው። ጣልያን እኮ በሸዋ ላይ ያነጣጠረው የጥላቻ መርዙ እንዳልበጀው ስላወቀ ሸዋ፣ ሸዋ የሚለውን ትቶ አማራ፣ አማራ በሚል አዲስ የጥላቻ መዝሙር ነው ድኅረ ዓድዋ የተከሠተው። ክንፈ ዳኘው ሕጻን ሆኖ ጡት ሲጠባ የሰማውን እንደያዘ ነው የጃጀው። ወይስ የጎንደርና የወሎን መሬት (ወልቃይትና ራያን) መርቁልን እና እንገንጠል ሲል ሸዋን አይከፋውም ብሎ ቆምሮ ይሆን?
ለማንኛውም ትግራይ የኢትዮጵያ ናት፤ ኢትዮጵያም የትግራይ ናት። ኢትዮጵያ ለትግራይ ብቻ የሆነ መሬት የላትም፣ የትግራይ ያልሆነ መሬትም የላትም። ዮዲትን ሸሽቶ ሸዋ የገባውም አክሱማዊ ነው፣ እዚያው የቀረውም አክሱማዊ ነው። አክሱም የአስክሱሞች የወላይታዎችም ነው። የመለስን የልጅነት ባንዳዊ ድንቁርና በእስተርጅና ማቀርሸት ለክንፈ እድሜ አይመጥንም።
ምንድነው? ወርቅ ወርቅ ሲባል ነበር፣ ከዚያም አልፎ ዳይመንድ፣ ነዳጅ ወይስ ታንታለም ተገኘ እንዴ? ፈረንጆቹ እንደሆነ ኮንጎ ሊያደርጉን እያንጃባቡን ነው። የማእድን ክምችት በያለበት አንዳንድ የጎበዝ አለቃ መንግሥት ሊያቋቁሙ። ዮክሬይንም አቧራው ሲዘቅጥ የማእድን ቁፋሮ ሆኖ ተገኘ አይደል የግርግሩ መዳረሻ? እግዚኦ!
ትግራይን “ሕየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ” (በአባቶችሽ ምትክ ልጆች ተወለዱልሽ) የምንልበትን ዘመን እንዲያመጣላት እንጸልይ እንጂ በአሮጌ ባንዶች ዲስኩር ሌላ ገደል እየተቆፈረላት ነው። እየተቆፈረልን ነው።