ድሮስ ፤  ከእባብ እንቁላል እርግብ ይገኛልን ??? – ሲና ዘ ሙሴ

ድሮስ ፤  ከእባብ እንቁላል እርግብ ይገኛልን ?

“በሲና ተራራ
በዛ በከፍታ
በዙፋንህ ሆነህ
ክብርህን አየነው ”

ያኔ ከሲና ተራራ የመጣው አይነት መልዕክት ፤ ለዛሬው ዓለም በእጅጉ ያሥፈልጋል ።

ስለ ተራ ሞቹ ሰው ማን ደንታ አለው ? መንግሥታት እንደሆነ አእምሮአቸው የተያዘው በዝና ነው ። ያውም በሞላጫ ዝና ። ዝና ሞላጫ ነው ። ትላንት ለህዝብ  ያሥተዋወቀህ ፣በከፍታ የናኘው  ዝናህ  ነገ ምደር ላይ ተከስክሶና አልባሌና መሳቂያ ሆኖ ታገኘዋለህ ። ነገ ሥልህ በዘመን ብዛት እጅግ የራቀውን ፣ የነጎደውን  ነገ ነው ። ከ10 ትውልድ በኋላ  ያለውን ነገ ። በዛ ነገ ፣ የማንኛውም መንግሥት ዝና ይረሳል ። …

በነገ ዕይታ ፣ ህይወት እንቆቅልሽና ድራማዊ ናት ።

ደሞም ተገንዘብ ፣ በህይወት ዑደት ውስጥ  ሰው ከትንሾ ትል የሚለይበት የህይወት ዕደት የለም ። ሰው እና ትል በህይወት ዑደት ተመሳሳይ ሽክርክሪት ነው ያላቸው ። ይወለዳሉ ፤ ያድጋሉ ፤ ይምታሉ ። ( ሳያድጉ የሚሞቱ ወይም የሚቀጩ ህይወቶች በሁለቱም ወገን እንዳሉም ይታወቃል ። )

በመወለድ ፣ በማደግ እና በመሞት ደረጃ ሰው ከትል እኩል ነው ።

ይኽ እውነት ቢሆንም በማህበራዊ ኑረው የበለጠ ትል የሚያደርጉት እውነቶች ደግሞ አሉ ።

አንደኛው እንደትል  ተነጂነቱ ነው ። ልምጭ እና እሥር ቤት ያለው መንግሥት ሰውን በየቀኑ እንደትል ሲነዳው እናያለን ።

ለምሣሌ ፣ በሚያሳዝን መልኩ ከፊሉ የኢትዮጵያ ህዝብ ፣ ከደርግ ሥርዓት ጀምሮ ሳይወድ በግዱ በየጎጡ መንግሥት እያስፈራራው ለድጋፍ እና ለተቃውሞ ሰልፍ እንደ ትል ወጥቶ ይርመሰመሳል ። በተለይም በኦሮሚያ ክልል ። ተራው ህዝብ ካድሬዎች የፃፉትን ወረቀት ይዞ በግድ በአደባባይ እንዲወጣ እና በማይገበው ቋንቋ ከቲባዎቹ ዘፍነውበት ወደ ቤቱ ይመለሳል  ። በነሱ ቤት የቀደመን ጭቆና እና ትምክህት በተመሳሳይ መልኩ መመለስ ፍትሃዊ ና ዴሞክራሲያዊ ነው ።  ። ይጮኻል ። ምንም ባልገባውና በማያውቀው ጉዳይ ውስጥ ገብቶ እንዲፈተፍት ይደረጋል ።  ባልገባው ጉዳይ “ በግንቦት ሃያ “  ለመከላከያ ድጋፍ ለማድረግ ሰልፍ ወጣ ይባላል ።

ይህ የለየለት ሸፍጥና የጅላንፎ ፕሮፓጋንዳ ነው ። ዛሬም “ አብይ መራሹ ፣ የብልፅግና  መንግሥት “ እንደ ወያኔ እና እንደ ደርግ በውሸት ፕሮፓጋንዳ የሚያምን  መንግሥት የሆነው ከሥሪቱ የተነሳ እንደሆነ አውቃለሁ ። ያልተዘራ አይታጨድምና !  ( መቼም አብይ አህመድ በአንድ እጁ ማጨብጨብ አይችልም ። )

በአንድ እጅ ማጨብጨብ ባይቻልም ፣ ጠ/ሚ  አብይ አህመድ የአገር መሪ በመሆኑ ሁሉም አካባቢ ፣ ጎጥና ቀበሌ ውስጥ ሳይቀር ፤ በሚጠፋው ጥፋት ጣታችንን ወደ ሰውየው  መቀሰራችን አይቀርም ። የህግ አሥፈፃሚው ቁንጮ በመሆኑ !

ዛሬ አብይ አህመድን በመልካም የሚያነሰው እጅግ ጥቂት ሰው ነው ።  በተደጋጋሚ ከህዝብ ፍላጎት ውጪ በወሰነው ውሳኔ የተነሳ ከህዝብ ጋር ተጣልቷል ። አንዳንድ ክልሎች ውሥጥ ያለው ህዝብም   ከወገኖቹ ሥደተሰ ፣መፈናቀልና ምት የተነሳ   አምርሮ ጠልቶታል ።  እርሱ ግን ዛሬም ህዝብን በግዳጅ ( ለቅንጥብጣቢ ሲሉ በሚጮሁ ምሥኪነሰ ህድ አደሮች እየታገዘ … ) በኦሮሚያ ክልል በግድ  ሰልፍ በማሶጣት ፣ “ ህዝብ ለመከላከያ ያለውን ድጋፍ ገለፀ “ ቀማለት ፕሮፖጋንዳ ይሰራል ።

ህዝብ የአገር መከላከያን መቼ ጠልቶ ያውቃል ? ” መከላከያ ማለት የኢትዮጵያ ህዝብ ልጅ ማለት አይደለም ወይ ? ”

በእውነቱ መንግሥት ውሥጥ ከትል ያልተሻሉ ሰዎች ናቸው የተሰገሰጉት ማለትም ይቻላል ። ዛሬ አሰስና ገሰሱ ነው መንግሥት የሆነው ። ይህንን የምታረጋግጡት ስራዬ ብላቸሁ የኦሮሚያ ከተሞች ምሽቶች ምን አሰንደሚመሥሉ ስታዩ ነው ።

“ በኦሮሚያ  ክልል ከተሞች  በምሽት ፣ ዘራፊዎች ሥለዘረፋቸው ሳያፍሩ በየመሸታ ቤቱ  ያወራሉ ።  እጅግ ጉድ የሚያሰኝ የዘረፋ ፣ የመሬት እና ቤት ሽያጭ  ታሪክ ያወራሉ ። ከሁሉም የመንግስት ተቋማት በጨረታ ሥም ፣ በግንባታ ሥም  በተሽከርካሪ ጥገና እና ነዳጅ ሥም  ረብጣ ብሮች ተሞጭልፈው  የሚመነዘሩት ና የቃል ኪዳን ውል የሚፈረምባቸው  በፍየል ቀርጥ ቤቶች እና በትልልቅ ሥጋ ቤቶች ውሥጥ ነው  ። ነጋዴዎች በሥጋ እና በመጠጥ ሥም እጅግ የሚዘገንን ዝርፊያም ያካሂዳሉ ። … ( የአገር ውሥጥ ገቢ ሰብሳቢ ቀረጡ ላይ በደንብ ይያዝልን ። እንላለን ። )

ባይገርማችሁ ፣ አንዳንድ እጅግ ያጌጡና በመብራት ያሸበረቁ  የፍየል ሥጋ መሸጫ ቤቶች   ፣   ጥብሥ  ብቻ ሳይሆን  ዝሙትም  ያቀርብላችኋል ። አንዳንዴም ካላሥተዋላችሁ ፣ የፍየል ጥብስ ብለው የሚሸጥላችሁ   ፤  የከረመ የበሬ ሥጋ ነው ። በሥካር ልብ ልታውቁ አትችሉምና ! !  እንኳን የበሬ ሥጋ ይቅርና ጨጓራ የበዛው የበሬ ሥጋ ቢቀርብላችሁ ወይም አንጀት ተቀላቅሎ በደበዘዘ መብራት ቢሰጣችሁ ከመብላት ውጪ አማራጭ የላችሁም ። (  አይጥ ጠብሰው ቢሰጧችሁም በፍየል ጥብስ ሥም በስካር መንፈስ እንክት አድርጋችሁ ትበላላችሁ ። )

በአንዳንድ   የመዝናኛ ቤቶችም የመጠጡ  ጥራት እጅግ የሚያጠራጥራችሁ …ለጤና ማጣት የሚዳርጋችሁ …በውስኪ ሥም የተቀላቀለ አረቄ የሚቀርብላችሁ ። በቢራ ሥም ከዚህ እና ከዛ የተበወዘ ጭላጭ የያዘ ጠርሙስ በግርግር የሚቀርብላችሁ መሆኑንን አታስተውሉም ። …

ይኽንን ማጭበርበር መቆጣጠር ያለበት ህግ አሥፈፃሚው  ግን የዕለት ከዕለት ሥራውን አይከውንም ። በህግ ማሥከበር ሥምም  ከሁለት ሰዓት በኋላ  ኪሱን ለማስከበረ በትጋት የተዘጋጀ ፣ ፖሊሥ ከጎጥ ሲቪል ግብረ ሃይልና በህዝብ  መዋጮ የተቀጠረ ሚሊሻ ጋር በየአሥፓልቱ ተሰማርቶ ይገኛል ። …

በየቀበሌው ሁሉም ሚሊሻ ና ፖሊስ ከወዶ ገቡ ሲቪል ሴትና ወንድ ጋር በአብረቅራቂ ልብስ ተከፍኖ    ወጪ ወራጁን በመፈተሽ ፣ መኪና አሥቁሞ በመበርበር መንገደኛን ያንገላታል ። ባሥ ሲልም ፣ ” የውሃ መግዣ ፤ የብርድ መከላከያ ፤ ስጡኝ ። ”  እያለ ይቀፍላል ። ( አይደረግም ካልክ ድርጊቱ ያጋጠማቸውን የብሾፍቱ ባለሥልጣናት ጠይቅ ። የብሾፍቱ ከተማ መግቢያ ፍተሻ ከአዳማ የተሻለ እና በፖሊስ ብቻ የሚደረግ መሆኑንንም እወቅ ። )

አንዳንዱን ከተማ በተለይም ከአዳማ ጀምሮ ያለውን ሥታሥተውል ፤ ይኽ አገር የአልሻባብ አገር ነው እንዴ ? በሰላማዊ አገር አሥፓልት ላይ የሚፈጠር ህገ ወጥነትን በእንደዚህ አይነት ፍተሻ መከላከል ይቻላል እንዴ ? ህገ ወጦችስ ፍተሻ መኖሩን እያወቁ በአሥፓልት መንገድ እንዴት ደፍረው ይጓዛሉ  ? ህገ ወጦችን ፣ ሌቦችና ዘራፊዎችን የሚቆጣጠር  የሚያድን …ልዩ ግብረ ሃይል መንግሥት ፣ እንደመንግሥት እንዴት ማቋቋም አቃተው ? ብለህም ትጠይቃለህ ።

ምላሽህም ድሮስ  የጃጁና ያውና አንድ የሆኑ ፣  ሆዳም ና ዘረኛ ካድሬዎችን ሰብስቦ ፣ ይኽንን ታላቅ ና በለምጡቅ አእምሮ ህዝብ በድፍረት  የሚመራ ፓርቲና   መንግሥት ከዚህ በላይ ምን ማድረግ ይችላል ? የሚል ጥያቄ አዘል መልስ ይሆናል ?

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

”አንድ እናርግህ ሲሉ፤መጀመሪያም አልተለያየንም በላቸው” | ፍራሽ አዳሽ | ጦቢያ |

Next Story

 ” አንበሳ ለማጥፋት ደኑን ለዕሳት” እንዳንሰሳት ?   

Go toTop