ሱዳን በኢትዮጵያ ሠራዊት ተገድለውብኛል ባለቻቸው ወታደሮቿ ምክንያት ተቃውሞዋን ለመግለጽ በአዲስ አበባ የሚገኙትን መልዕክተኛዋን ወደ ካርቱም መጥራቷ ተዘገበ።
የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ ሰኞ፣ ባለፈው ሳምንት ረቡዕ ዜጎቹ በሱዳን ግዛት ውስጥ ተይዘው ወደ ኢትዮጵያ ከተወሰዱ በኋላ ተገድለዋል በማለት ከሷል።
ይህንንም በማስመልከት የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሰኞ ከሰዓት በኋላ ባወጣው መግለጫ፣ ግጭቱ የተከሰተው በህወሓት ድጋፍ የኢትዮጵያን ድንበርን አልፈው በገቡ የሱዳን መደበኛ ወታደሮች መሆኑን በመግለጽ የሱዳንን ክስ አጣጥሎታል።
ሱዳን ግን ለክስተቱ ኢትዮጵያን ተጠያቂ በማድረግ ተቃውሞዋን ለመግለጽ አምባሳደሯን ከአዲስ አበባ ከመጥራቷ በተጨማሪ በካርቱም የኢትዮጵያን አምባሳደር መጠራታቸው ተገልጿል።
ሱዳን በአገሯ የሚገኙትን የኢትዮጵያን አምባሳደር የጠራችው በአወዛጋቢው ድንበር አካባቢ ተፈጽሟል ስላለችው የወታደሮቿ ግድያ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሯ አመልክቷል።
እንዲሁም የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ስለ ክስተቱ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ይፋዊ ቅሬታውን ለማቅረብ እየተሰናዳ መሆኑንም ተጠቅሷል።
ሱዳን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት፣ ምርኮኛ የነበሩ ሰባት ወታደሮቿን እና አንድ ሲቪል ገድሏል ስትል በመከላከያ ኃይሏና በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል ክስ አቅርባለች።
BBC