የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት እንደሚደግፍ እና በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካን ጣልቃ ገብነት እንደሚያወግዝ የኤርትራ ሕዝብ ነፃነት ግንባር አስታወቀ፡፡
የግንባሩ ዋና ፀሐፊ አል-አሚን ሙሐመድ አሊ ይህን ያስታወቁት የኤርትራ አብዮትን 60ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ ከኤርትራ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ነው፡፡
አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ በምትከተለው የተዛባ ፖሊሲ እና በምታደርገው ጣልቃ ገብነት ምክንያት የቀጣናው ሀገራት በግጭት መታመሳቸውን ቀጥለዋል ብለዋል፡፡
ሀገራቸው ኤርትራ የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት እንደምትደግፍ እና በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ የአሜሪካን ጣልቃ ገብነት እንደማትቀበለው አረጋግጠዋል፡፡
“የአፍሪካ ቀንድን ለመበታተን ይፈልጋሉ፤ በሶማሊያ ያደረጉትን እና ዛሬም በኢትዮጵያ እያደረጉት ያለውን ተመልከቱ፤ በኢትዮጵያ ውስጥ እየሆነ ስላለው ነገር ምን ያገባቸዋል፤ ይህ የውስጥ ጉዳይ አይደለምን?” ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡
አሜሪካ በኤርትራ እና በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እየገባች ያለችው አሸባሪው ህወሓትን ዳግም ወደስልጣን ለማምጣት ያላትን ፍላጎት ስለማይቀበሉ ነው በማለት ይመልሳሉ፡፡
በኢትዮጵያ የሚፈጠር አለመረጋጋት በጥቅሉ በቀጣናው ሰላም ላይ በተለይ ደግሞ በኤርትራ ሰላም ላይ ቀጥተኛ ስጋት ይደቅናል ነው ያሉት፡፡
የአሜሪካ አጀንዳ የአፍሪካ ቀንድን መበታተን ነው፤ የእኛ ምርጫ ደግሞ ከኢትዮጵያ፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን እና ጅቡቲ ጋር በትብብር በመስራት ሰላምን ማረጋገጥ ነው ብለዋል
የኤርትራ ሕዝብ ነፃነት ግንባር ዋና ፀሐፊ አል-አሚን ሙሐመድ አሊ፡፡