አንድ ሱስ አለብኝ (ዘ-ጌርሣም)

October 1, 2020

አለብኝ አንድ ሱስ የሚያስለፈልፈኝ
ኢትዮጵያ እናት ሀገር እያለ እሚያስጮኸኝ

አውሊያ እንዳለበት ሰው
ተይዞ በመተት እንደ ተቀየደው
እየደጋገመ የሚያስለፈልፈኝ
መሳቂያ እስከምሆን በቀን የሚያስጮኸኝ
ተኝቸ ከእንቅልፌ የሚቀሰቅሰኝ
የምግብ ፍላጎት የሚከለክለኝ
አንድ ነገር አለ ሰላም የሚነሳኝ
እኔም አውቀዋለሁ
ተገንዝቤዋለሁ

አለብኝ አንድ ሱስ የሚያስለፈልፈኝ
ኢትዮጵያ እናት ሀገር እያለ እሚያስጮኸኝ

ሐኪም በመድኃኒት
ጠንቋይ ባለው መተት
የሃይማኖት መሪ በሚያደርሰው ፀሎት
ዳኛ ህግ ጠቅሶ በሚሰጠው መብት
ሊያክመኝ
ሊያሞኘኝ
ቀርቶ ሊያሳምነኝ
በህግ ሊዳኘኝ
ጭራሽ የማይቻል
ይሁን እንኳን ቢባል
ገና በልጅነት
በፀዳው ወረቀት
ሁሉን በሚቀበል
ነገር ሳይቀላቅል
ከፍቅር በስተቀር
ክፋት ሳይሸነቁር
ይሉኝታን እምነቱ
ቅንነት ኩራቱ
ሀገር ማለት እናት
ወኔ የአባት ዕትብት
የሕዝብ አንድነት
አብሮ ኑሮ መሞት
በጋራ መደሰት
ልዩነት አብሮነት
የአንድነት መሠረት
ብሎ የሚያስጮኸኝ
አንድ ሱስ አለብኝ
ብዬ የሰየምኩት የሕዝብ መድኃኒት
ፍቱን የተባለ የፍቅር ክትባት

አለብኝ አንድ ሱስ የሚያስለፈልፈኝ
ኢትዮጵያ እናት ሀገር እያለ እሚያስጮኸኝ

ሰው ገና አልገባውም
ቆይቶ ቢቆጨውም
ምንም ይዘግይ እንጅ ኋላ ላይ ይደርሳል
አዋቂ ለመባል ካለፈ ይቀላል
ከሱስ ለመላቀቅ
ከውድቀት ለመራቅ
ከፀፀት ለመዳን
መወጣት የድርሻን
ይሆናል ማርከሻ
ወይም መቀነሻ
እኔ ምን ቸገረኝ
ሰው ያለኝን ቢለኝ
ጭራሽ ሊያብስብኝ
ከሱስ ላያድነኝ
ወደዱም
ጠሉትም

አለብኝ አንድ ሱስ የሚያስለፈልፈኝ
ኢትዮጵያ እናት ሀገር እያለ እሚያስጮኸኝ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

ባለቤቱ ያቀለለውን አሞሌ ባለዕዳው አይቀበለውም – አምባቸው ደጀኔ

Next Story

ዛሬ ሌላ ቀን ነው!! – አንድነት ይበልጣል – ሐዋሳ

Go toTop