እሁድ ግንቦት 17/2006
ሀገራችን ኢትዮጵያ የበርካታ ሙስሊሞች መገኛ መሆኗ አያጠያይቅም! ሆኖም ዛሬ ላይ ያሉ ሹማምንቶች ሙስሊሞችን እና እስልምናን መብቱን በመንጠቅ ታላቅ በደል እየፈፀሙበት ይኸው በርካታ አመታት ተቆጠሩ፡፡ ይህንንም ኢፍትሃዊነት እና በደልን በግልፅም በስውርም እንዳሻቸው ሲያደርጉ ተዉ የሚላቸው ሰው ባለመኖሩ በርካታ ኢ-ፍትሃዊነቶችን ሲፈፅሙብን በትእግስት እና በጥበብ ሲያሳልፉ የነበሩት በርካታ አባቶች እና እናቶች በአፄው ዘመን፣ ብሎም በደርግ ዘመን ታግለው እና መስዋትነትን ከፍለው የሃይማኖት ነፃነትን አስከብረው አለፉ፡፡ አላህ መልካም ስራዎቻቸውን ይቀበላቸው! ምንጊዜም አላህ (ሱ.ወ) ከህዝብ መካከል ለዲኑ (ለእምነቱ) የሚቆረቆሩ ጀግኖችን ይፈጥራል፡፡ በየዘመናቱ እና በየቦታዎቹ በርካታ ጀግኖችን ፈጥሯል፤ ወደፊትም ይፈጥራል፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ ልክ የዛሬ 23 አመት ከጨቋኙ የደርግ ስርአት ተገላግላ ህዝበ ሙስሊሙም በመጠኑም ቢሆን እምነቱን በነፃነት የሚያራምድበት አየር አግኝቶ ነበር፡፡ ሆኖም ብዙም ሊቆይ አልቻለም፡፡ መንግስት በደርግ ጊዜ ተገኝቶ የነበረውን የመጅሊሱን ተቋም አመራሮች ለስልጣን መሳሪያ በማድረጉ ተስፋ ተጥሎበት የነበረው የኢትዮጵያ ሙስሊሞች እድገት ካለፉት ስርአቶች በባሰ ሁኔታ ተዳክሞ እና ነፃነቱን ተነጥቆ ሲበደል ቆይቶ ነበር፡፡ ሲቀጥልም በገዢው መንግስት እና በመጅሊሱ ጋብቻ የተነሳ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች እድገት በመታፈኑ እና መጠነ ሰፊ የአስተዳደር ችግር በመከሰቱ በማህበረሰባችን ላይ ይህ ነው የማይባል ሰፊ ችግር ተስተናገደ፤ በዋናነት የአንድነት ችግር እና የድርጅታዊ መዋቅሮች አለመኖር! ችግሮችም በሂደት ተበራከቱ፡፡
ለረጅም ጊዜ እነዚህን ችግሮች በግልፅ የሚቃወም ህዝብ ባለመኖሩ ህብረተሰቡ በውስጡ ሲያፍነው የነበረውን በደል የአወሊያ ወጣት ተማሪዎች በይፋ ያሰሙት ጀመር! ‹‹አሻዕብ ዩሪድ ኢስቃጠል መጂሊስ!›› ሲሉ በእልህ፣ በቁጣና በለቅሶ ለኢትዮጵያ ሙስሊሞች ደወላቸውን አሰሙ፡፡ በአራቱም አቅጣጫ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ወደ አወሊያ ተመሙ፡፡ የተማሪዎቹንም ቁጣ ተቀላቅለው አዜሙ፡፡ ከህዝቡ ውስጥም የተመረጡ በሳል 17 ኮሚቴዎች ራሳቸውን ለህዝብ ሊሰጡ ተመረጡ፡፡ ቁጣው የገነፈለው ድፍን የኢትዮጵያ ሙስሊሞች በተከታታይ ጁሙአዎች ከህዝብ በወጡ ታላላቅ ዳዒያን በመመራት በአወሊያ፣ ብሎም በበርካታ ክፍለ ሀገራት፣ ብሎም በውጭ ሀገራት በእኩል ድምፀት እና በአጭር እና ቀላል 3 ጥያቄዎች በህብረትና በአንድነት ለመታገል ቃልኪዳን ተጋቡ፡፡ እነዚህ ብርቅዬ ወንድሞቻችን እና ዳኢዎቻችን፣ እንዲሁም የሀገር ሽማግሌዎች ህዝቡ እንደ አይኑ ብሌን የሚሳሳላቸው፣ በሀገራዊ ፋይዳቸው በርካታ ማህበረሰቦችን የሚጠቅሙ ከህዝብ የወጡ የህዝብ ልጆች መሆናቸውን በአንዋሩ የሀምሌ 7 እና 8 አገር አቀፍ የሰደቃና አንድነት ላይ አሳዩ፡፡ በሚሊዮኖች ታጅበው ሚሊዮኖችን ለሰላም ዘብ እንዲሆኑ መሪ ሆኑ፡፡ ሚሊዮኖችን ሰላማዊ ትግልን አስተማሩ፡፡
ይህን ያደረጉት ውዶቹ ብርቅዬ ኮሚቴዎቻችን ሊታሰሩ እንደሚችሉ እና በርካታ ስቃዮችን ሊቀበሉ እንደሚችሉ አስቀድመው ተናግረዋል፡፡ የተናገሩትም ደረሰ፡፡ ብርቅዬዎቹን ኮሚቴዎቻችንን እና አጋረሮቻቸውን አሰሩብን፡፡ በማእከላዊ ከፍተኛ ስቃይን አስተናገዱ፡፡ በኢፍትሃዊው የካንጋሮ ፍርድቤት ለኢፍትሃዊ ድራማ ለሁለት አመት ተመላለሱ፡፡ ያም ሆኖ ግን አሁንም ከህዝብ እንዳልወጡ እና የህዝብ እንደሆኑ አሳይተዋል፡፡ ህዝበ ሙስሊሙም በፅናት አብሯቸው ዘልቋል፡፡
አሁን እነዚህ ውድና ብርቅዬ ኡስታዞቻችን እና ዱአቶቻችን በፍርድ ሂደት የመከላከያ ምስክራቸውን እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡ ህዝቡም ‹‹እንመሰክራለን›› ሲል ከቤቱ ወጥቶ እያጀባቸው ይገኛል፡፡ እስከመጨረሻው የፍርድ ሂደት አብሮ ሊዘልቅ የገባውን ቃልኪዳን አድሷል! አላሁ አክበር!
የሐሰት ከስ አይገዛንም!
ትግላችን እስከድል ደጃፎች ይቀጥላል!
ድምፃችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!