የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት ስምንት ወራት ከኦፕሬሽን እና ከተለያዩ አገልግሎቶች ለማግኘት ያቀደውን ገቢ እንዳላሳካ ሰንደቅ ጋዜጣ ከአዲስ አበባ ዘገበ። እንደ ዘገባው ከሆነ አየር መንገዱ ከሐምሌ 1/2004 እስከ የካቲት 30 ቀን 2005 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት 30 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ገቢ ለማግኘት አቅዶ ማሳካት የቻለው 25 ቢሊዮን ብር (82 በመቶ) ያህሉን ብቻ ነው።
ከትራንስፖርት ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው በያዝነው በጀት ዓመት ስምንት ወራት በሀገር ውስጥ በረራ 231 ሚሊዮን (የዕቅዱን 95 በመቶ) የመንገደኞች መቀመጫ ለማቅረብ እንዲሁም 407 ሺህ (የዕቅዱን 99 ነጥብ9 በመቶ መንገደኞችን ማጓጓዝ የተቻለ ሲሆን፣ በውጪ አገር በረራ 16 ነጥብ 7 ቢሊዮን (የዕቅዱን 91 በመቶ) መንገደኞች መቀመጫ ለማቅረብ እንዲሁም 3 ነጥብ 1 ሚሊዮን (የዕቅዱን 87 በመቶ) መንገደኞችን ማጓጓዝ ተችሏል።
በተመሳሳይ መልኩ በጭነት አገልግሎትም 553 ሚሊዮን ቶን ኪሎ ሜትር የጭነት አገልግሎት ሽያጭ (የዕቅዱን 99 ነጥብ 9 በመቶ) ማከናወን መቻሉን መረጃው ይጠቁማል።
አየር መንገዱ ያስመዘገበው የኦፕሬሽንም የፋይናንስ አፈፃፀም በአቪየሺን ኢንዱስትሪው የሚስተዋለውን ጠንካራ የገበያ ፉክክር ተቋቁሞ ያስመዘገበው በመሆኑ ትልቅ ስኬት ነው ሲል ሚኒስቴሩ ጠቅሷል። (ሰንደቅ ጋዜጣ የዛሬ ኤፕሪል 17 ዕትም)