![]()
የፍትህ ሚኒስቴር ዛሬ አርብ ታህሳስ 29 ምሽት ባወጣው መግለጫ፤ በእነ ጃዋር መሐመድ መዝገብ ስር ያሉ 20 ተከሳሾች እና በእነ እስክንድር ነጋ መዝገብ ስር ያሉ አራት ተከሳሾች ክሳቸው እንዲነሳ መደረጉን አስታውቋል። የተከሳሾቹ ክስ እንዲነሳ የተደረገው “ሃገራዊ የምክክር መድረክ ሂደት ውጤታማነት እና አካታችነት ከፍ ለማድረግ በማሰብ” መሆኑን ሚኒስቴሩ ገልጿል።
በተመሳሳይ ሁኔታ በእነ ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል መዝገብ ክስ ከቀረበባቸው 62 ግለሰቦች እና ድርጅቶች ውስጥ የስድስት ግለሰቦች ክስ እንዲነሳ መደረጉን ሚኒስቴሩ በዛሬ ምሽት መግለጫው ጠቅሷል። “የጤና እና የዕድሜ ሁኔታቸውን ከግምት በማስገባት” ክሳቸው እንዲነሳላቸው የተደረጉት አቶ ስብሐት ነጋ፣ ወ/ሮ ቅዱሳን ነጋ፣ አቶ ዓባይ ወልዱ፣ አቶ አባዲ ዘሙ፣ ወ/ሮ ሙሉ ገብረ እግዚአብሔር እና ወ/ሮ ኪሮስ ሐጎስ ናቸው።
በእነ ጃዋር መሐመድ እና ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል መዝገብ የተካተቱ ተከሳሾችን ማንነት ለመመልከት ከታች የተያያዙትን ምስላዊ መረጃዎች ይመልከቱ።
(ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)