ቀን የካቲት 2017
በአንዳርጋቸው ጽጌ
- ከአጻጻፍና ከይዘት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች

ሀ) የቅርጽ ጉዳይ
የማንበብ ባህል እየተዳከመ መጥቷል። በመሆኑም ሰፊ ትንታኔ የሚጠይቁ ጉዳዮችን በአጭሩ ጨምቆ ማቅረብ እንደሚያስፈልግ ተረድቻለሁ። የአማራ ህዝብ የሚገኝበት ሃገረ ኢትዮጵያና፣ ሃገረ ኢትዮጵያ የምትገኝበት ቀጠና ከየትኛው አካባቢ የበለጠ የተወሳሰቡ ዘርፈ ብዙ የሆኑ ችግሮች ያሉበት ነው። በዛ ላይ እየተወሳሰበ የመጣው የቅርብና የሩቅ መንግስታትና ሃገራት እንዲሁም የአለም አቀፍ ኩባንያዎች ጂኦ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጎት የቀጠናውን ችግር በማባባስ የሚጫወተው ሚና አለ። እንዲህ አይነት የተወሳሰቡ ሃገራዊ፣ ቀጠናዊና አለምአቀፋዊ ተጽእኖዎች ባሉበት አካባቢ የአማራ ህዝብ የሚያደርገውን የህልውና ትግል በሚገባ ለመተንተን እንኳን ረጃጃም ጽሁፎች አይደለም የዳጎሱ መጽሃፍትም ቅም የሚሉት አይደለም።
ችግሩ ግን በሚገባ ያልተማረው ብቻ ሳይሆን የተማረ የምንለውም፣ መጽሃፍ አይደለም ረጃጃም ጽሁፎችን ማንበብ ካቆመ ቆይቷል። ቀደም ብሎም ቢሆን ማንበብ መጻፍ የማይሆንለት የኢትዮጵያ ሆነ የአማራ ምሁር፣ እድሜ ለማህበራዊ ሚድያ መጻፉንም ማንበቡን እርግፍ አድርጎ ትቶታል።
ምሁሩ ሳይቀር ከሙያው ውጭ የቀረችውን የማወቅ ፍላጎት የሚያረካው ዘመን ያመጣቸውን የተግባቦት መሳሪያዎች ከድንቁርና በመጣ ድፍረት ተቆጣጥረው ያሻቸውን የሚናገሩበትን የዩትዩብ፣ የቲክቶክ የትዊተር፣ የፊስቡክና የኢንስተግራም ሸቃጮችን በማዳመጥ ሆኗል። ይህ ሁኔታ፣ እጅግ አደገኛ የሆነ ከእውቀት የተጣላ በስሜት የሚነዳ፣ የግብስብስ መረጃዎች ሱሰኛ (የጃንክ መረጃዎች ጃንኪ a junkie for junk information ) ፈጥሯል። ይህን ባህል ግምት ውስጥ በማስገባትና ፈረንጆቹ “ለአሮጌ ውሻ አዲስ ትሪክ ማስተማር አይቻልም” የሚሉትንም ብሂል በመጋፋት እኔም በተቻለ መጠን የወቅቱን የአማራ ህዝብ የህልውና አደጋ ምልከታዎቼን የራሳቸው አርስት ባላቸው አጫጭር ጽሁፎች አማካይነት ለማቅረብ ተገድጃለሁ።
ለ) ጽሁፍ ለማን የተጻፈ ነው?
ይህ ጽሁፍ የተጻፈው በአማሮች መሃከል መደረግ ለሚገባው ውይይት ነው። የታሪክና የግል ህይወት ምጸት በሚመስል መልኩ እነዚህን ቃላቶች የዛሬ 32 አመት “ የአማራ ህዝብ ከየት ወዴት” በሚል ርእስ ባሳተምኳት ትንሽ መጣጥፍ ውስጥ መገኘታቸው አስገርሞኛል። በገጽ 5 መጨረሻ ላይ” የዚህ ጽሁፍ አላማ አንድና አንድ ብቻ ነው። ዛሬ በሃገራችን ውስጥ ባለው ሁኔታ በተለይም የአማራውን ህዝብ በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ በአማራውና በአማራው ውስጥ ብቻ መደረግ ላላበት ውይይት የራሳችንን መንደርደሪያ ሃሳቦች ለማቅረብ ነው” ይላል። በዚህ ጽሁፍ ላይ አማራ ያልሆኑ አስተያየት ቢሰጡበት ማስቆም አይቻልም። በበኩሌ ከጽሁፉ ጋር በተያያዘ የሚነሱ ጥያቄዎች እና አስተያየቶች ካሉ ምላሽ የምሰጠው ከአማሮች ለሚመጡት ብቻ ነው።
አማሮች ስል በአማራ ፋኖ የሚመራው የአማራን የህልውና ትግል ፍትሃዊ ነው ብሎ የሚያምን ማንኛውም ሰው ማለቴ ነው። እንዲህ ከሆነ ማኛውም ኢትዮጵያዊ የአማራን የህልውና ትግል ፍትሃዊነት ከተቀበለ አማራ ነው። የአማራ ቁስል ቁስሌ፣ ህመሙ ህመሜ ነው በማለት በድርጊቱ እኔም አማራ ነኝ እያለን ስለሆነ። እንዲህ አይነቱ ግለሰብ ጥያቄ ቢጠይቀኝ ለመመለስ ቢሞግተኝ ለመሞገት ዝግጁ ነኝ። ከዚህ ውጭ አንድ ግለሰብ ዘርማንዘሩ እስከምንጅላቱ አማራ መሆኑን ሊቆጥር ይችላል። በድርጊት ግን እንደ ዳንኤል ክብረት፣ ዳኛቸው አሰፋ፣ በለጠ ሞላ፣ አረጋ ከበደ፣ ተመስገን ጥሩነህ፣ አገኘሁ ተሻገር፣ ብናልፍ አንዱ አለም እና ሌሎችም የንጉስ አብይ አህመድ የቤተ መንግስት ባሪያ ሆኖ እስከመጣ ድረስ አማራ ሊሆን አይችልም። በእንዲህ አይነቱ ፍጥረት ለመጠየቅም ወይም ለመሞገትም ፈቃደኛ አይደለሁም።
ንጉስ አብይ ባቋቋማቸው፣ ለሆዳቸው ባደሩ ባሪያ የሚድያ ጄነራሎቹም በሚመሩ የማህበራዊ ሚድያዎችና ሰራዊቶቻቸውም ለመጠይቅ ፈቃደኛ አይደለሁም። ይህ ጽሁፍ በዋንኛነት ማንን ቀንድ ሊያስበቅል እንደሚችል ሰለማውቅ የኦሮሞ ብልጽግና የሚድያ ሰራዊት እና ጸረ አማራና ኢትዮጵያ ሃይሎች የአማራ ስም እየተጠቅሙ ዘመቻ እንደሚከፍቱበት ግልጽ ነው።
እንደተለመደው የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይ ደግሞ የአማራ ህዝብ “ደሃ እንጂ ደደብ አይደለም” በሚል የህዝብ መተማመን ላይ ቆሜ እውነትን በድፍረት መጻፍ ግድ የሚል ሆኖ አግኝቸዋለሁ ።
በበኩሌ የዚህን ጽሁፍ ጉዳይ “በአማሮችና በአማራ ወዳጆች መሃል ለሚደረግ ውይይት” በሚል ያጠርኩት ከማንም ለሚነሳ ማናቸውም ጥያቄ ወይም አስተያየት ምላሹን መስጠት ወይም ሃሳቡን ማስተናገድ ከባድ ስለሆነ አይደለም። ያለንበት አዋካቢና አሰቃቂ ሁኔታ የሚያቀናጣ የትኩረትና የጊዜ የተትረፈረፉ እድሎች ስለማይሰጠን ብቻ ነው።
የሚገርመውና አሁንም የታሪክና የግል ህይወት ምጸት ይመስል፣ ቀደም ብዬ በጠቀስኳት መጣጥፍ ላይ የዛሬ 32 አመት፣ የአማራ ህዝብ ወከባ ውስጥ መሆኑን፣ በፍጥነት መንቀሳቅስ እንዳለብን የሚገልጽ ቃላቶች መጠቀሜ ራሴን አስገርሞኛል። ያች ትንሽ መጣጥፍ እዛው ገጽ 5 ላይ “የአማራ ህዝብ ……… ራሱን በፍጥነት ማዘጋጀት ካልቻለ፣ ይህ ህዝብ በሚሊዮኖች በረሃብ የሚረግፉበት፣ በሚሊዮኖች የሚሰደድብት፣ እንደ ህዝብ ክብሩ፣ ነጻነቱና ህልውናው ከማይጠበቅበት ሁኔታ ውስጥ እንደሚገባ መጠራጠር አይኖርብንም” ብላ ነበር። ህልውና የምትለውን ቃል ልብ በሏት።
አሁንም ልክ እንደ ዛሬ 32 አመቱ የአማራ ህዝብና ከዚህ ህዝብ አብራክ ነው የወጣሁት ብሎ የሚያስብ ምሁር፣ ትኩረትን ሳይበታትኑ እንደሌዘር አነጣጥሮ ስራን እየለዩ አድምቶ መስራት የሚጠይቅ እጅግ አሳሳቢ የሆነ ዘመን ውስጥ መገኘነቱን መረዳት አለበት።
በ32 አመታት ውስጥ ለአማራው በበጎ መልኩ የተቀየረ ነገር የለም። የባሰ እንጂ። በመሆኑም ነው እርባና በሌላቸው፣ መሬት ላይ ያለውን በአማራ ህልውና ላይ ያሰፈሰፈውን መአት በፍጥነት መፍትሄ በመስጠት አስተዋጽኦ በሌላቸው የትኛዎቹም አጀንዳዎች ላይ፣ ማንኛውም ህልወናዬ አደጋ ላይ ወድቋል ብሎ የሚያምን አማራ መጠመድ የለበትም የምለው። “በጉንጭ እና ብእር አልፋ ምልልሶች የሚጠፋ ጊዜ ሊኖረን አይገባም ።
ሐ) የጽሁፉ ይዘት በተመለከተ
ይህ ጽሁፍ ራሳቸውን በቻሉ የተለያዩ፣ ነገር ግን ተያያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ላይ ያተኩራል። ሁሉም ጉዳዮች ላይ የተሰጡ ምልከታዎች የግልና የምር ናቸው። አንዳቸውም ለማምታታትና ለማሳመን (to confuse and convince) የተጻፉ አይደሉም። ሁሉም ጉዳዮች ሰፊ ትልልቅ ርእስ የተሰጣቸው ቢምስልም አሁን በቀጥታ የአማራ ህዝብ ከሚያደርገው የህልውና ትግል ጋር በተያያዘ ቅኝት የተጻፉ ናቸው። የሃሳብ ቦርጭ እንዳይኖራቸው አድርጌ ለማቅረብ ሞክሪያለሁ። ጽሁፉ በሚከተሉት 13 ርእሶች የተከፋፈለ ነው።
- ያለፈው እና መጪው ዘመን ለአማራ፤
- የአማራ የህልወና ትግል የአማራ ታጋዮች የጋራ ግንዛቤ፤
- የአማራ ትግልና የፋኖ ማኒፌስቶ
- የአማራ የህልውና ትግል፣ አማራ ልሂቅ፣ አማራነትና ኢትዮጵያዊነት
- የ1960ዎቹ ትውልድና አማራነት የአማራ ህልውና ትግል
- ህብረ ብሄራዊ የሆነው የጸረ ወያኔ ትግል እና አዲሶቹ የአማራ ብሄረተኞች
- በአማራ አሸናፊነት ላይ የተመሰረተ የአማራ ህዝብ የህልውና ማስከበር ክንውን፣ ሃገራዊ ቀጠናዊና አህጉራዊ አንደምታው
- ወዳጅ ማብዛት ጠላትን መቀነስ የአማራ ስትራተጂ
- የአማራ ህዝብ የህልወና አደጋ ምንጮች ብዙ ናቸው። ሁሉን አደጋዎች በአንድ ጊዜ መጋፈጥ አይቻልም።
- የፋኖ አመራር አንድነት፣ የዳይስፖራ ድጋፍና አንድነት ትስስር
- የአማራ የህልወና ትግል በጤነኛ እና በታመሙ ብሄረተኞች እንቃስቃሴ ላይ ያሳደረው ተጽእኖና አንደምታው።
- የአማራ ህዝብ ለህልውና መከበር የሚያደርገው ትግልና ኤርትራ፣
- የአማራ ህዝብ የህልውና ትግል የመጠንም የአይነትም እመርታ እንዲያሳይ፤
ለሚቀጥሉት 13 ተከታታይ ቀናት ከዚህ በላይ በዘረዘርኳቸው ርእሶች የጻፍኳቸውን ጽሁፎች በፌስቡክና በትዊተር ገጼ አጋራችኋለሁ ተከታተሉ። ለሌሎችም አጋሩ