ዶ/ር አብይ አህመድ የሀገራችን ሙስሊሞች እና ሌሎችም ኢትዮጵያውያን እንደ ሁል ጊዜው በመውሊደል ነቢ በዓልም የነበሩንን የሰላም፣ የመረዳዳት፣ የመከባበር እና የመጠያየቅ ባሕል በማስቀጠል የበኩላችቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቀረቡ:: ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ያሉት የነቢዩ መሐመድ የልደት በዓል አስመልክቶ ባስተላለፉት መል ዕክት ነው::
የመልዕክቱ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ይቀርባል:
በኢትዮጵያና ከኢትዮጵያ ውጭ ለምትኖሩ መላው የእስልምና ተከታይ ወገኖቼ፤ እንኳን ለ1493ኛው የነቢዩ መሐመድ(ሰ.ዓ.ወ) የልደት በዓል በሠላም አደረሳችሁ፡፡
በእስልምና የወራት አቆጣጠር ራቢአል አወል በሚባለው በሦስተኛው ወር በ12ኛው ቀን በየዓመቱ የሚከበረው ይህ የልደት በዓል በተለምዶ በእኛ ሀገር መውሊድ ወይም መውሊደል ነቢ በመባል የሚታወቅ ሲሆን ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ወጣት፣ ዐዋቂ፣ ሕጻን፣ ወንድ፣ ሴት፣ ከተሜ፣ ባላገር፣ የተማረ፣ ያልተማረ፣ ሀብታም፣ ድኻ፣ ሙስሊም፣ ክርስቲያን ወዘተ. ሳይለይ የሚያሳትፍ ከመሆኑም ባሻገር፣ በመኖሪያ ቤት፣ በመስጊድ እንዲሁም በእስልምና የመድረሳ ት/ቤቶች በተለያዩ የእምነቱ ሥርዓት የሚካሄድ መሆኑ ይታወቃል፡፡
ኢትዮጵያውያን ሙስሊም ወገኖቻችን በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች በድምቀት የሚያከብሩት ይህ የመውሊደል ነቢ በዓል በሙስሊሙ ብቻ ሳይሆን በመላ ኢትዮጵያውያን በጋራ የሚከበር ወደ መደመር የፍቅር ሰገነት ከፍ ያለ ልዩ በዓል ነው፡፡ በኢትዮጵያችን በሙስሊሙ በዓል ክርስቲያኑ፤ በክርስቲያኑ በዓል ዋቄፈታው፤ በኢድ- በፋሲካው -በመውሊድ በገናው እና በእሬቻው የእንኳን አደረሰህ፣ እንኳን አደረሰሽ ቅብብሉ የማንለያይና የተዛመድን መሆናችንን አጉልቶ የሚያሳይ ነው። መስተጋብራችንም መልካም ምኞት እስከታከለበት ዝይይር በሚዘልቅ የፍቅር ሸማ ተከብክቦ ወደፊትም ደምቆ ይቀጥላል፡፡
መውሊደል ነቢ በመሠረታዊነት ነቢዩን እና በነቢዩ አማካኝነት ለዓለም የወረደውን የእስልምና አስተምህሮቶች በመዘከር ለሕፃናት በትረካ የሚተላለፍበት በዓል ሲሆን የዲኑ ኡለማዎችም በግጥምና በመንዙማ ለፈጣሪያቸው ምስጋና በማቅረብ ያሳልፉታል፡፡ ዕለቱን በበጎ ሥራ፤ በምጽዋት፣ የተመረጡ የቁርአን ክፍሎችና የመውሊድ ምንባብ በመስማት ፣ የመንዙማ ፕሮግራሞች በማካሄድ ከዚያም አልፎ የተቸገሩን በመርዳትና የታመሙትን በመጠየቅ፣ ብሎም ራሳችንን ከክፉ ተግባራት በማራቅ እምነታችንን የምናጠናክርበትም ዕለት ነው፡፡
በመሆኑም መላ የሀገራችን ሙስሊሞች እና ሌሎችም ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ እንደ ሁል ጊዜው በመውሊደል ነቢ በዓልም የነበሩንን የሰላም፣ የመረዳዳት፣ የመከባበር እና የመጠያየቅ ባሕል በማስቀጠል የሀገራችንን ሁለንተናዊ ለውጥ እና ሕዳሴ ለማረጋገጥ የበኩላችሁን እንድትወጡ በዚህ አጋጣሚ ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡
በመጨረሻም በዓሉ የሰላም፣ የፍቅር፣ የይቅርታ እና የመደመር በዓል እንዲሆንላችሁ ከልብ እመኛለሁ፡፡
መልካም የልደት በዓል!!