(ዘ-ሐበሻ) በኢትዮጵያ ያለው ወቅታዊ ሁኔታ ከ እለት ወደ እለት ወደ አስጊ ደረጃ እየደረሰ ይገኛል:: ከሰሜን እስከ ደቡብ ከምስራቅ እስከ ምዕራብ ግጭት በየቦታው እያስተናገደች ባለችው ኢትዮጵያ አለመረጋጋቱ አይሏል:: ዛሬ በሃሮማያ ከተማ ሕዝብ አደባባይ በመውጣት የሕወሓት አስተዳደርን ሃገራችንን ለቃችሁ ውጡ በሚል ተቃውሞውን ሲያሰማ ውሏል::
በሃሮማያ በተደረገውና በርካታ ወጣቶች በተሳተፉበት በዚህ ሰልፍ “ወያኔ ሌባ” ሲሉ የተቃወሙት ወገኖች የሃገሩ ባለቤት ኦሮሞ ነው ሃገሩን ለቃችሁ ውጡ ሲል ተቃውሞውን ከፍ ባለ ድምጽ አሰምቷል::
ገንፍሎ የወጣውን የሕዝብ ቁጣ ለመቆጣጠር የሕወሓት መራሹ መንግስት በአካባቢው ወታደሮችን እንዳሰማራም ለዘ-ሐበሻ የደረሱ መረጃዎች ሲገልጹ እስካሁን በሰውና በንብረት ላይ ስለደረሰ ጉዳት የገለጹት ነገር የለም::
በሌላ በኩል የሕወሓት ልዩ ፖሊስ በም ዕራብ ሓረርጌ ዶባ ወረዳ 3 ወገኖችን መግደሉ ተሰማ:: እንደ አካባቢው ምንጮች ገለጻ ኢብራሂም አብዲ፣ ሮባ ዳዲ እና ለጊዜው ስሙ ያልተገለጸ አንድ ወገን ናቸው በሕወሓት ልዩ ፖሊስ የተገደሉት::
በአካባቢው ውጥረት ነግሷል – ዘ-ሐበሻ ጉዳዩን ተከታትላ ለመዘገብ ትሞክራለች::