ትናንት ዘ-ሐበሻ በሰበር ዜና መምህር ግርማ ወንድሙ መታሰራቸውን መዘገቧ አይዘነጋም:: ፖሊስ ዛሬ መምህር ግርማን ፍርድ ቤት አቁሞ ጠርጥሮ ያሰረበትን ምክንያት አስረድቷል:: የፌደራሉ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 1ኛ የወንጀል ችሎት በመምህር ግርማ ላይ ፖሊስ የፈጸመውን ክስ ከሰማ በኋላ ፖሊስ አቶ ግርማ ቢፈቱብኝ መረጃና ሰነዶችን ሊያሸሹ ይችላሉና 14 ቀን ይፈቀድልኝ ሲል ጠይቋል:: የመምህር ግርማ ጠበቃ የተጠረጠሩበት ክስ ዋስትና የሚያስከለክል አይደለም ሲል ሲል በዋስ እንዲለቀቁ ጠይቆ ነበር:: ሆኖም ፍርድ ቤቱ ፖሊስ አብዛኛውን ምርመራ በማጠናቀቁ የጠየቀውን 14 የምርመራ ቀን ሰርዞ በ7 ቀን ውስጥ አሉኝ የሚላቸውን ማስረጃዎች አሰባስቦ እንዲጨርስ ፈቅዶ ውጤቱን ለመስማትም ጥቅምት 25 2008 ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል። መምህር ግርማ ወደ ማረፊያ ቤት ሄደዋል::
በመምህር ግርማ ወንድሙ ላይ የቀረበው ክስ የሚከተለው ነው:- (ከመንግስት ሚዲያዎች እንደወረደ የተገኘ ነው)
የወንጀሉ ዝርዝር
ፖሊስ መምህር ግርማ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት የሆነው ወንጀል የተፈፀመው መስከረም 2006 ዓ.ም ነው ብሏል።
በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ወሰን ግሮሰሪ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚኖሩት አቶ በላይነህ ከበደ በመምህር ግርማ የማታለል ወንጀል የተፈጸመባቸው ግለሰብ ናቸው።
እንደ ፖሊስ የምርመራ መዝገብ እኚህ ግለሰብ ከትዳር አጋራቸው ጋር 400 ካሬ ሜትር ላይ ባረፈ መኖሪያ ቤታቸው ይኖሩ ነበር።
እንደ ምርመራ መዝገቡ መምህር ግርማ የግል ተበዳይን እምነት በመጠቀም የምትኖርበትን መኖሪያ ቤት እስከ ጥር 30 2006 ሽጠህ ካልወጣህ አስከሬንህ ይወጣል ይሏቸዋል።
የፖሊስ የምርመራ መዝገብ እንደሚለው ልጅ ያልወለዱት ባልና ሚስት ከመሞት መሰንበት በማለት ይህንን ቤት በጣም በዝቅተኛ ዋጋ በ800 ሺህ ብር ይሸጡታል።
ቤቱ በዚህ ዋጋ እንዲሸጥ መምህር ግርማ በራሳቸው ሰዎች አማካኝነት ብዙ ያልተገባ ስራ ሰርተዋል ነው የሚለው የምርመራ መዝገቡ።
ከዚያም መምህር ግርማ በዚህ ብቻ ሳይመለሱ የግል ተበዳዩን ቦሌ አካባቢ በራዕይ ያየሁት ቦታ አለ እዚያ ነው ገዝተህ የምትኖረው ይሏቸውና ሌላ የማታለያ ዘዴ ቀየሱ ይላል ምርመራው።
ቤቱ የተሸጠበትን 800 ሺህ ብር አምጣና እንዲበረክትልህ ልፀልይበት ብለው በመውሰድ በዚያው ውለው አደሩ፤ የግል ተበዳዩም በእርሳቸው ላይ ያላቸው እምነት ባለመጥፋቱ በትዕግስት ስልክ ቢደውሉላቸውም ስልካቸው ዝግ ሆነባቸው፤ ይባስ ብሎ ከሀገር ወጡ ተባለ የሚለውም ተጠቅሷል።
የግል ተበዳይ ሁኔታው ማታለል መሆኑን ስለተረዱ 2007 መጋቢት ወር ገደማ ለፖሊስ ያመለከቱ ሲሆን፥ እርሳቸው ከሄዱበት እስኪመለሱ ፖሊስ የግል ተበዳዩን እና የምስክሮችን ቃል ተቀብሎ ቆይቶ ተጠርጣሪው መምህር ግርማ ወንድሙን ትናንት በቁጥጥር ስር አውሏቸው ነው ዛሬ ፍርድ ቤት ያቀረባቸው።
ተጠርጣሪው መምህር ግርማ እኔ የተባለውን ሰው ቀይ ይሁን ጥቁር አይቼው አላውቅም፤ ሆን ተብሎ ከጀርባ የተጠነሰሰብኝ ሴራ አለ በማለት ለችሎቱ አስረድተዋል።