የመንግስቱ ኃይለማሪያም ጭካኔ እና የአንጋፋው ደራሲና ጋዜጠኛ አቤ ጉበኛ አሟሟት – በጥበቡ በለጠ

February 9, 2025

የካቲት 1 ቀን 1972 ዓ.ም

#በዛሬዋ_ዕለት

ከ 45 ዓመት በፊት ልክ በዛሬዋ ቀን አንጋፋው ደራሲና ጋዜጠኛ አቤ ጉበኛ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየበት ዕለት ነበር።

ደራሲና ጋዜጠኛ አቤ ጉበኛ

ታሪኩ 45 አመታት ወደኋላ በምዕናብ ያስጉዘናል። ቀኑ ቅዳሜ ምሽት ነው፡፡ ወሩ የካቲት 1 ቀን 1972 ዓ.ም ቦታው ደግሞ አዲስ አበባ ጐጃም በረንዳ አካባቢ፡፡ ታላቁ ኢትዮጵያዊ የጥበብ ሰው አቤ ጉበኛ ቀበሌ 34 አካባቢ ከአስፋልቱ ዳር ተዘርግቶ ወድቋል፡፡

ጐጃም በረንዳ አካባቢ የሚኖሩ አቤን የሚያውቁ ሰዎች ተጠርተው መጡ፡፡ አቤ ‘‘አንሱኝ፣ አንሱኝ፣ ተጠቃሁ…’’ እያለ ያቃስታል፡፡ የመጡት ሴቶች ናቸው፡፡ ሊያነሱት ሞከሩ፡፡ ጐተቱት፡፡ ሊሳካላቸው አልቻለም፡፡ ሌሎችም ተሰበሰቡ፡፡ ኃይል ሲገኝ አነሱት፡፡ ከዚያም የወሰዱት ሆስፒታል አልነበረም፡፡ አቤ ቀደም ብሎ ‘‘አርባ ምንጭ’’ የሚባል ሆቴል ውስጥ መኝታ ክፍል ተከራይቷል፡፡ እናም ወደ መኝታ ክፍሉ ወስደው አስተኙት፡፡

ሲነጋ ማለትም እሁድ ጠዋት ፖሊሶች መጥተው ወደ ጳውሎስ ሆስፒታል ወሰዱት፡፡ ሆስፒታል ከገባ ከግማሽ ሰዓት በኋላ ዶክተሮቹ አቤ ጉበኛ መሞቱን አረጋገጡ፡፡ ‘ተጠቃሁ’ እያለ ሲያቃስት የነበረው አቤ ጉበኛ ማን መታው? ምን ሆኖ ሞተ?

ሞቱ ከተነገረ በኋላ ቀብሩ ታሰበ፡፡ ማን ይቅበረው? ከ20 መፃህፍት በላይ ያሳተመ ጐምቱ ደራሲ ቀባሪ አጣ፡፡ ማን ደፍሮ ሬሳውን ወስዶ ይቅበረው? ማዘጋጃ ቤት ሊቀብረው ዝግጅት ላይ እያለ ሲራክ ቀለመወርቅ የተባሉ ሰው ‘አቤን ቀበርሁና አልቀበርኩኝ ምን እንዳልኮን ነው ብዬ ቆርጬ ገባሁበት’ ብለው ገቡበት፡፡ በኋላም አስከሬኑ መመርመር አለበት ብለው በፖሊስ ወደ ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ተወሰደ፡፡ ተመረመረ፡፡ ውጤቱ ምን ይሆን? አቤን ምን ገደለው?

ከምርመራው በኋላ አቤ ጉበኛ መቀበር አለበት፡፡ የጐጃም ወዳጆቹ ተባብረው አስከሬኑን ወደ ትውልድ ቦታው ወሰዱት፡፡ ከዚያም ማክሰኞ የካቲት አራት ቀን 1972 ዓ.ም በባህርዳር አውራጃ በአቸፈር ወረዳ ይስማላ ጊዮርጊስ ገዳም ተቀበረ፡፡

በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ እጅግ ደማቅ ከሚባሉት ጥበበኞች መካከል አንዱ የሆነው አቤ ጉበኛ በምን ምክንያት ሞተ የሚለው ጥያቄ ሳይመለስ ለዘመናት ቆይቷል፡፡ ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የገባውና የተመረመረው አስከሬኑም ውጤቱ እንዳይነገር ታፍኖ ለረጅም አመታት ተቀመጠ፡፡ በዘመኑ የነበሩት የፖሊስ መርማሪዎች ፖሊሳዊ ግዴታቸውን ሳይወጡ ቀሩ፡፡በዚህም ታሪክ ይወቅሳቸዋል፡፡

የአቤ ጉበኛ ብዕር ለኢትዮጵያ ህዝብ እና ለሀገረ ኢትዮጵያ እድገትና ስልጣኔ የሚታትር ነበር፡፡ ይሁን እንጂ እሱ ሲሞት ደግሞ ሁሉም ዝም አለ! ሃቀኛ ደራሲ አድናቂዎች እንጂ ወዳጆች አይኖሩትም የሚለው የበአሉ ግርማ አባባል እውነት ነው፡፡ እናም የአቤ ጉበኛ ሞት ተደፋፈነ፡፡ ደሙን የሚጠይቅለት ጠፋ!

‘‘ኮከብ’’ የተባለ መጽሔት 1ኛ አመት ቁጥር 1 1985 ዓ.ም ላይ ያወጣውን ፅሁፍ ስለ አቤ ጉበኛ የህይወት ታሪክ የሚያወሳው መጽሐፍ ይዘክራል፡፡ እንዲህም ይላል፡፡‘ ‘የልጆቹ እናት የልብስ ሻንጣውን ከ3ኛ ፖሊስ ጣቢያ በተረከቡበት ወቅት በግድያ ተጠርጥረው የታሰሩ ለጊዜው ማንነታቸው ያልታወቀ ሦስት ግለሰቦች እንደነበሩ ቢገለፅላቸውም ብዙም ሳይቆዩ ተጠርጣሪዎች በመንግስት ትዕዛዝ ተፈትተዋል፡፡

ከዚህ በኋላ ውሾን ያነሳ ውሾ ይሁን’’ ሆነና ቄሱም መጽሐፉም ዝም አሉ፡፡… እንዴት ሞተ? የሚለውን ጥያቄ ግን የትኛም ክፍል አላነሳም፡፡ ብቻ አልፎ አልፎ ሰዎች አፋቸውን አቀራርበው በሚኒሞ ማንሾካሾካቸው አልቀረም፡፡ ታዲያ ዙሪያቸውን በሚገባ ከቃኙ በኋላ ነው በዝቅተኛ ድምፅ ‘‘አቤን መንግስት ነው የገደለው’’ የሚሉት፡፡

የአቤ ጉበኛ ገዳይ በይፋ አልታወቅ አለ፡፡ እንደውም የደርግ ሊቀመንበር እና የሐገሪቱ ፕሬዝዳንት የነበሩት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም አደናጋሪ ንግግር አደረጉ፡፡ የአቤ ጉበኛን ገዳይ እንዳይታወቅ ሆን ብለው መሸሸግ ፈለጉ፡፡ እናም ቅዳሜ ህዳር 27 ቀን 1973 ዓ.ም ለኢትዮጵያ ህዝብ ንግግር ያደርጉ ነበር፡፡ ንግግሩ ደግሞ የተደረገው የኢትዮጵያ ህፃናት ቀን ሲከበር ነው፡፡

ኮሎኔሉ በንግግራቸው መሐል ስለ ሟቹ ደራሲ አቤ ጉበኛም ጣል አደረጉ፡፡ እንዲህም አሉ፡-‘‘አብዮቱ ህፃናትን ከረሐብ፣ ከበሽታ፣ ከትምህርት ጥማት ብቻ ማስጣል ሳይሆን ከእንዲህ አይነቱ ርህራሄ ከሌለው ተፅእኖ እና የተሳሳተ አመለካከት ማዳን ይኖርበታል፡፡… በዚህ ረገድ ዛሬ ከመካከላችን የማይገኝው በጊዜው ተጨባጭ ሁኔታና ባለው ፀረ-ፊውዳላዊ አቋም ‘አልወለድም’ የተሰኘ ድርሰቱን ለኢትዮጵያ ህዝብ አበርክቶ የነበረውን የሟቹን የአቤ ጉበኛን አባባል ያስታውሰናል” እያሉ መንግስቱ ኃይለማርያም ተናግረዋል፡፡

በቅኔ ሊናገሩ የፈለጉት እኔ አልገደልኩትም ነው፡፡ ግን አያሌ ማስረጃዎች የእርሳቸው መንግስት አቤን እንደገደለው ይመሰክራሉ፡፡ ምክንያቱም እንደ ኤልያስ አያልነህ ጥናት መንግስታዊ የሆነው አዲስ ዘመን ጋዜጣ ራሱ የአቤን ሞት በአጭር ዜና የዘገበው ከተቀበረ ከዘጠኝ ቀናት በኋላ ነው፡፡ ለዚያውም በወቅቱ የነበረው የደራሲያን ማኀበር ባደረገው ውትወታ እና ጉትጐታ ነው ዜናው የተሰራለት፡፡

ለመሆኑ ዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ገብቶ የነበረው የደራሲ አቤ ጉበኛ የአስከሬን ምርመራ የት ደረሰ? ደርግ 17 አመታት ከገዛ በኋላ ወደቀ፡፡ ኢሕአዴግ ገባ፡፡ አዲስ መንግስት ተመሰረተ፡፡ ተዳፍኖ የኖረው የአቤ ሞት በልዩ ልዩ ጋዜጦችና መጽሔቶች ይፃፍበት ጀመር፡፡ ኤልያስ አያልነህ ደግሞ የአቤ ጉበኛን ብእራዊ ተጋድሎ በሰፊው ይሰራበት ገባ፡፡

አቤ ጉበኛ ከሞተ ከ 19 አመታት በኋላ የዳግማዊ ምኒልክ የአስከሬን ምርመራ ውጤትን በመጽሐፉ አትሞት አወጣው፡፡ የአቤ አስከሬን ምርመራም ይፋ ሆነ፡፡ ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ የተተረጐመው ውጤት እንዲህ ይላል፡-

➺ የሟች ስም፡- አቤ ጉበኛ

➺ ዕድሜ:- 41

➺ ፆታ:- ወንድ

➺ የሬሳ ቁጥር፡- 445/7

➺ የምርመራው ቀን፦ 3/6/72

➺ ዜግነት፡- ኢትዮጵያዊ

➺ አድራሻ፡- አዲስ አበባ

➺ የውጭ ሰውነት ምርመራ ውጤት፡- መጠኑ 3×4 ሴንቲ ሜትር ሆኖ የተቆረጠ ቁስል ግራ እግሩ ላይ ታይቷል፡፡ በቀኝ በኩል በሚገኘው የመሐል ጭንቅላቱ ቆዳ ላይ የተፋቀ ቁስለት አለበት፡፡ በቀኝ በኩል በሚገኘው የመሐል አንጐል ውስጠኛ ሽፋን ክፍሉ ስር 7x5x8 ሴንቲ ሜትር መጠን ያለውና ደም የቋጠረ እብጠት አለበት፡፡ አንጐሉ ውስጠኛ ሽፋን ክፍል ብዙ ደም አለበት፡፡ አንጐሉ አብጧል፡፡

በአጠቃላይ ለሞት ያበቃው፡- ስለት በሌለው (በድልዱም) መሳሪያ ጭንቅላቱ ላይ በመመታቱ ምክንያት ብዙ ደም የቋጠረ እብጠት ታችኛው አንጐል ሽፋን ክፍል ሥር በመከሰቱ ነው፡፡

አቤ ጉበኛ የተገደለው በሰው እጅ ነው፡፡ ያ ሰው ደግሞ ከደርግ መንግስት በተሰጠ ትዕዛዝ የፈፀመው እንደሆነ ይገመታል፡፡ ምክንያቱም አቤ ጉበኛ ከቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት ጀምሮ እስከ ደርግ አገዛዝ ድረስ እጅግ ሀይለኛ የሆኑ ፖለቲካዊ ፅሁፎችን እና ቴአትሮችን እየፃፈ ሰፊ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ መንግስታትን በድፍረት በመናገር፣ ለኢትዮጵያ ይጠቅማታል የሚለውን አስተሳሰቡን ምንም ሳይፈራ በግላጭ የሚፅፍ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ደራሲ ነው።

#ታሪክን_ወደኋላ #TariknWedehuala

© በጥበቡ በለጠ

 

የግንቦት 8 ቀን 1981 ዓ.ም የመፈንቅለ መንግስት ተሳታፊዎች የፍርድ ችሎት ሂደት ፤

2 Comments

  1. ይህ መረጃ በእርግጥ ትክክል ነው ወይ? መጣራት ያለበት ጉዳይ ይመስለኛል። ዓመተ ምህረቱስ በአማርኛ ወይስ በእንግሊዘኛ? ግልጽ አይደለም። እኔ እስከማውቀው ድረስ፣ ተሳስቼ ልሆን እችላለሁ፣ ደራሲ አቤ ጉበኛ የፊዩዳሉን ስርዓት የሚተችና አብዮቱ ከመፈንዳቱ በፊት እንደተገደለ ወይም እንደ ሞተ ይነገራል። ሞቶ የተገኘውም አንድ ሆቴል ቤት ውስጥ ሲሆን ምናልባት የንጉሱ የፀጥታ ኃይሎች እንደገደሉት ይነገራል። ለማንኛውም ይህ ነገር በሚገባ መጣራት ያለበት ይመስለኛል።

  2. አቤን ከደርግ ጥርስ ያስገባው ብዙ ጉዳዪች ቢኖሩም። በዋንኛነት የሚጠቀሰው ፓለቲካና ፓለቲከኞች የተሰኘው ድራማ ነክ መጽሃፉ ነው። በነገር በተጎሸመ ቁጥር ለሁሉም ምላሽ መስጠት የሚወደው የብዕር ፓለቲከኛው አቤ ለጎነተሉት ብቻ ሳይሆን መጣጥፋቸው ላላማረውም ቆንጣጭ ምላሽ በመስጠት ይታወቃል።ይህ ባህሪው ጥቂትም ቢሆን ከዪሃንስ አድማሱ ጋር ያመሳስለዋል። በዚህ ባህሪውም ሆነ በሌላ ጉዳይ ጥርስ ተነክሶበት እንደነበረ በጊዜው በህይወት የነበሩና በቅርብ የሚያውቁት ይናገራሉ። በዚህ ላይ “መሬት የማን ነው” በሚለው መጣጥፉም የሚጠሉትና የሚያሞካሹት ነበሩ። ግራም ነፈሰ ቀኝ አቤ የሞተው በደርግ ዘመን እንጂ በንጉሱ ጊዜ አልነበረም። እርግጥ ነው አቤ በታህሳሱ ግርግር ሳቢያ ዘብጥያና ግዞት ወርዶ እንደነበረ አብረውት የነበሩት እንደ ኮ/ሌ እምሩ ወንዴ የመሳሰሉት መስክረዋል። የተገደለው ግን በንጉሱ ጊዜ አይደለም። እንዲያውም በንጉሱ ጊዜ አሜሪካ ነው የነበረው። ሃገሬ ህዝቤ ወገኔ ምድሬ ብሎ ተመልሶ ሂዶ ነው ተቀጥቅጦ የተገደለው። ስለሆነም በንጉሱ ጊዜ ነው የተገደለው የሚለው ወሬ ከእውነት የራቀ ነው።
    አብዪት ልጆቿን ትበላለች እያለ ራሱ አብዶ ሌላውን አሳብዶ በመሳሪያ አፈሙዝ ሁሉን አምበረክካለሁ ያለው የወታደር መንጋ በህዝባችን ላይ የፈጸመው በደል ሰማይ ጠቀስ ነው። የለውጡ ረመጥ 1966 – 1968 በሚል ርዕስ ሻለቃ ጌታቸው የሮም ደርግ የራሱን ወታደራዊ አመራሮች ገድሎ ዞሮ ተመልሶ ጸረ አብዪት በሚላቸው ሃይሎች እንደተገደሉ አድርጎ ያቅርብ እንደነበር በደርግ በሰውር የተገደሉ ሰዎችን ስም ዝርዝር ጨምሮ አስፍሯል። በእኔ እምነት ዳኛቸው ወርቁ፤ ብርሃኑ ዘሪሁን ሌሎችም ያለጊዜአቸው የተለዪን ደራሲያን ሁሉ በሰው እጅ እንጂ በበሽታ እንደሞቱ አላምንም። እውነተኛ ኢትዮጵያዊያንን የሚያጠፉ ሃይሎች ብዙ ናቸው። ቀዳሚው ግን ደርግ ነበር። በተጨማሪም በደርግ አመራር ሰርገው የገቡ የወያኔና የሻቢያ የከተማ አርበኞች ጭምር ተሳታፊዎች እንደነበሩ መረጃ አለ። የሻምላው ትውልድ የሚለውን መጽሃፍ ይመልከቱ! የኢትዮጵያን አንድነትና የህዝቧን ሰላም የሚፈልጉ ሁሉ እየታደኑ በሴራ ተለቅመው ተገለዋል። ታሞ ሞተ፤ መኪና ገጭቶ ገደለው፤ ገደል ገብቶ ሞተ፤ የት እንደገቡ አይታወቁም እየተባሉ ወደዛኛው ዓለም ያለ ጥፋታቸው ያሸለቡት ብዙ ናቸው።
    ህዝባችን ለመከራና ለጠኔ የሚዳርጉት እንደ ከሰል ካውያ ቶሎ ግለው የሚበርድት የሃገራችን ፓለቲከኞች ናቸው። ይሁን ያኔ በርዪተ ዓለም ሳቢያ ተጨራረስን። የአሁኑ ግን ካለፈውም የከፋ ነው። መደንፋት፤ መፎከር፤ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት። የእኔ ብሄር ከዛኛው ይልቃል እያሉ መተርተር የበሽታ እንጂ የጤና አይደለም። ይህ ሁሉ ጉራ ለበፊተኞችም አልጠቀመም። አሁን ላሉት አለቆቻችንም አይጠቅምም። በቅርቡ የኦሮሞው ፕሬዝደንት በጨፌ ኦሮሚያ ስብሰባ ላይ ያደረገውን ንግግር ሳዳምጥ ተገርሜአለሁ። ሰው እንዴት ሰከን ብሎ የዓለምንና የሃገር የፓለቲካ ንፋስን አይመለከትም። በጦር መሳሪያ ክምችትና ትጥቅ ቢሆን ኑሮ ደርግ ዛሬም በስልጣን ላይ በቆየ ነበር። ግን ያን ትጥቁን መልሶ ያስታጠቀው ለሻቢያና ለወያኔ ነበር። በጦር ሃይሉ ብዛት ደርግ አልዳነም። ተፈነቀለ። የፈነቀሉትም ተፈነቀሉ። ታዲያ እንዴት ለብልጽግና መንግስት ሁለቱ የቅርብ ጊዜ ጉዳዪች ትምህርት አይሰጡትም? ለዚህ ነው ያኔም አሁንም አተረማምሰው እግሬ አውጭኝ የሚሉት። የማይድን ፓለቲካ። ሰው በላ ፓለቲካ። ረሃብና ጠኔ፤ መከራና ስቃይ አዝናቢ ፓለቲካ። እልፈተ ቢስነት! አይሰለችም? ያለፈው የፓለቲካ ውስብስብ ዛሬ ላለንበት ውጥንቅጥ ሰበብ ነው። ስናሳዝን። ተደመሩ ተብለን ስንቀነስ። በማሳረጊያው አቤ ጉበኛ ዛሬም ወደፊትም ለእውነት በቆሙ ወገኖቹ ሲወሳ ይኖራል። ተወለድ፤ አልወለድም ነውና ነገሩ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

አማራ እንቅልፍህን ለጥጥ! ኦነግሸኔዎችም በዕቅዳቸው መሠረት እየሄዱ ነው!

Next Story

ችሮታ (በእውቀቱ ስዩም)

Go toTop