መልዕክተ ገና (መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ)

January 7, 2022

ሉቃስ 2

¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯

10 .  መልአኩም እንዲህ አላቸው፦ እነሆ፥ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ፤

11 . ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና ።

12 . ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ ።

13 . ድንገትም ብዙ የሰማይ ሠራዊት ከመልአኩ ጋር ነበሩ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ ፦

14 . ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ ።

* እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ ።

ሰውን ከሞት ወጥመድ ለማዳን ና በጎ ፈቃድን ለማንገስ ነው ክርስቶስ ኢየሱስ ወደዚች ምድር የመጣው ። ይሁን እንጂ ዓምላክ እንደጠበቀው በዚች ምድር በጎ ፈቃድ አልነገሰም ። ዛሬም የዳቢሎስ ጥፋት በሰው የዕለት ፣ ዕለት ጭካኔ ይገለፃል ።

ከዩናይትድ እስቴት ኦፍ አሜሪካ እስከ አውሮፓ ፤ ከኢሲያ እስከ ላቲን አሜሪካ ፤ ከአፍሪካ ፣ ከገልፍ አገሮች እስከ አውሥትራሊያ ሰው በግለኝነት ና በስግብግብነት አጥር ውሥጥ ራሱን በማኖሩ በዓለም ላይ በተለይም በአፍሪካ ና ከሳህራ በታች ባሉ አገሮች የሰው ሥቃይ በዝቷል ።

ከነዚህ ከገራት ውጪ ፣ በሶሪያ ፣ በየመን ፣ በሱማሊያ ፣ በሱዳን እንሆ ዛሬ ና አሁን በካዛክስታን ሴጣን   የሰውን  አእምሮ ተቆጣጥሮ  ይደንሳል ። እንዲህ ዓይነቱ አሥጠሊ ተግባር ሁሉ ከሰዎች መልካም ፈቃድ ማጣት የሚከሰት ነው ። ከዚ በታች ያሰፈርኩት በሉቃስ ወንጌል ላይ የተፃፈው ፣ የኢየሱስ ክርስቶስ የበጎ ፈቃደኝነት ተምህርት ሰው በምድር ላይ በሚቆይባት ጥቂት ቀን ቢተገብረው በሥጋ ና በነፍሱ የሚጠቅመው ነው ።

 

ሉቃስ 10

¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯

25 እነሆም፥ አንድ ሕግ አዋቂ ሊፈትነው ተነሥቶ፦ መምህር ሆይ፥ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ? አለው ።

26 . እርሱም፦ በሕግ የተጻፈው ምንድር ነው? እንዴትስ ታነባለህ? አለው ።

27 . እርሱም መልሶ፦ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም አሳብህም ውደድ፥ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ አለው ።

28 . ኢየሱስም፦ እውነት መለስህ፤ ይህን አድርግ በሕይወትም ትኖራለህ አለው ።

29 . እርሱ ግን ራሱን ሊያጸድቅ ወድዶ ኢየሱስን፦ ባልንጀራዬስ ማን ነው? አለው ።

30 . ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለ፦ አንድ ሰው ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ወረደ በወንበዴዎችም እጅ ወደቀ፤ እነርሱም ደግሞ ገፈፉት ደበደቡትም በሕይወትና በሞት መካከልም ትተውት ሄዱ ።

31 . ድንገትም አንድ ካህን በዚያ መንገድ ወረደ አይቶትም ገለል ብሎ አለፈ ።

32 . እንዲሁም ደግሞ አንድ ሌዋዊ ወደዚያ ስፍራ መጣና አይቶት ገለል ብሎ አለፈ ።

33 . አንድ ሳምራዊ ግን ሲሄድ ወደ እርሱ መጣ አይቶትም አዘነለት ፥

34 . ቀርቦም ዘይትና የወይን ጠጅ በቍስሎቹ ላይ አፍስሶ አሰራቸው፥ በራሱ አህያም ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማደርያ ወሰደው ጠበቀውም ።

35 . በማግሥቱም ሁለት ዲናር አውጥቶ ለባለቤቱ ሰጠና፦ ጠብቀው፥ ከዚህም በላይ የምትከስረውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ አለው ።

36 . እንግዲህ ከነዚህ ከሦስቱ በወንበዴዎች እጅ ለወደቀው ባልንጀራ የሆነው ማንኛው ይመስልሃል ?

37 . እርሱም፦ ምሕረት ያደረገለት አለ። ኢየሱስም፦ ሂድ አንተም እንዲሁ አድርግ አለው ።

ይሁን እንጂ ዓለም በዝንጋታ ገመድ ሥለምትጎትተን ሁላችንም የዛሬ ጥጋባችንን እንጂ የነገ ህመምን ፣ ሥቃይን ፣ የሞት ጣርን ወዘተ ። ድንገት እንደ ውሃ ሙላት እንደሚመጡብን ፈፅሞ አንገነዘብም ። እናም በዛሬው በታላቅ ምሥራች ና ከሞት ወጥመድ የመዳን ቀን  ፣ በዝንጋታ ገመድ ዓለም እንደምትጎትታቸው ለማያሥተውሉ ፣ በተግባር ቃሉን ለማይፈፅሙ ፣ በቃል ግን ወንጌልን ለሚያነበንቡ ፣  ከጳጳሱ ብሰው በአንደበታቸው ጤፍ ለሚቆሉ ፣  እምነት ና ኃይማኖትን መሸቀጫ ላደረጉ ሥለ እውነተኛው እምነት ና ኃይማኖት በግል በተረዳሁት ልክ ልፅፍ ወደድኩ ።

ወድሞቼ ሆይ ! ሰዎችን ፣ ” ቀናና በጎ ሁኑ ! ” ከማለቴ አሥቀድሞ እኔ ራሴ ከአሥርቱ የፈጣሪ ትዕዛዛት ሥንቱን እንዳከበርኩ እጠይቃለሁ ።( … )እናም ሐጢያተኝነቴን አምኜ ያለአንዳች ፍርሐት ከመኃሪው ፈጣሪ  ከኢየሱስ ክርስቶስ  ) ፊት በፀፀት እቆማለሁ ። እናም ይምረኛል ።  ሐጢያቴን ይቅር ይለኛል ። ያሥተሰርይልኛል ። የእኔ እምነት ሐጢያተኝነቴን ማመን ነው ።  ፃድቅ አይደለሁም ። እምነቴ እንደ ፈቃዱ መኖር ነው ።  ፈጣሪ በእኔ የሚተገብረው ፍቃድ አለው ። በእያንዳንዱ ፍጥረቱም የራሱ ፈቃድ አለው ።

አንተ ሰው ፣ ወደ ፈጣሪ ፊት ለመቅረብ ሁሉም ሰው መብት አለው ። ፀሎት ቻለ አልቻለ ። መሥፈርት የለውም ። ሰውኛ ነው መሥፈርቱ ። ፈጣሪ በቲኦሎጂ የፕሮፊሰር መዓረግ ሥላለህ ዘወትር አንተን አያዳምጥህም ። ወንድሜ ከእያንዳንዱ ፍጡር  አእምሮ ጋር የፈጣሪ መንፈሥ የተገናኘ ነው ። የተቆራኘ ነው ።የተቆላለፈ ነው ። ልክ እንደ ሸማኔ ድር ። ደሞም ፈጣሪ ሰው አይደለም ። የትም የሚገኝ ሁሉን ቻይ መንፈሰ ነው እንጂ ። ለሰው  ፊትም አያዳለም ና እኔንን ከሌላው ሰው አብልጦ አይወደኝም ። ኢየሱስ ፃድቃንን ፍለጋ አልመጣም ። ከፈሪሳውያንም ጋር አልበላም ና ጎስቋላውን እና ምሥኪኑን አላዛርን ከእኔ ይልቅ ይወደዋል ። ኢየሱስ ክርስቶስ የፈጣሪን አመለካከት ሊያሳየን ፈልጎ በምድር የ3 ዓመት ቆይታው ይኽንን አድርጓል ።  …

የሰውን ብልጣ ብልጥነት ፣ ጅልነት ና  የዘወትር የጠልፎ መጣል ሩጫውን ፣ የኑሮ ገመድ ጉተታውን፣ ክፋቱን ፣ ምቀኝነቱን ፣ ሥግብግብነቱን እዚህ  ማንሳት አያሥፈልገኝም  ። ደግሞም  በተሰጠው መክሊት ተጠቅሞ ሥለበለፀገውና መክሊቱን ቀብሮ ለከሰረው ሰው  ፣ ሰው ነኝ ና የምመክረው ምክር የለኝም ።… ደሞስ ፣ ለእያንዳንዱ  ሰው ፈጣሪ የሰጠው እንጀራ ላይ እኔን ማን ወጥ ጨላፊ አደረገኝ ?!

በበኩሌ ፣ ወጥ መጨለፍ የምፈልገው በህይወት ላይ ነው ። ሰው ከጥበብ ወጥ እያጠቀሰ ይበላ ዘንድ እንሆ እጋብዘዋለሁ ።..

ሰዎች ሆይ ! ሁላቸውም ታውቃላችሁ ።  በዓለም፣  የተለያዩ ኃይማኖቶች ና ኃይማኖተኞች እንዳሉ ። ብዙዎቹ በፈጣሪ መኖር የሚያምኑ እና ከሞት በኋላ ሁለተኛ የመኖር ዕድል አለ የሚሉ ናቸው  ። ሁሉም ኃይማኖቶች  ሐጢያትን ይከለክላሉ ። ሰዎች ግን ሐጥያትን በየቀኑ ይሰራሉ ። ላለመሥራት የሚጠነቀቁ  ብዙ አማኞች አሉ ። ግን ግን ጥንቃቄ  ሐጢያት ከመሥራት አይጠብቃቸውም ።በተግባር ባይሰሩም ፣ በአይንና በአንደበት ሐጢያትን  ሳይገነዘቡት ይሰራሉ  ።  በአንደበታቸው ሐጢያትን በየቀኑ  ሺ ጊዜ ይፈፅማሉ  ። ( አንደበት ክፉ ብልት ነው ፣ ማንም ሰው አይቆጣጠረውም ። ይላል መፀሐፈ ቁልቁሉ ። )

ቤተ ክርስቲያኖች  የክርስቶስን ትንሳኤ ዘወትር በአንደበታቸው በመሥበክ ፣ ” ሰው ከሞት በኋላ በመንፈሥ ይነሳና የፈጣሪ አገልጋይ ሆኖ ለዘላለም ይኖራል ። ” በማለት ለፅድቅ እንድንተጋ ያሥጠነቅቁናል  ። ሰው  ከሞት በኋላ እየዘመረ ። እያመሠገነ ። በዘላለማዊ ሐሴት ውሥጥ ከፈጣሪ ጋር የመኖር ዕድል ፈንታ  አለው እያሉ ተሥፋ ይመግቡናል ። ያለመሞትን በውሥጣችን እንድናረግዝ ያደርጉናል ።  በገነት እንወልደዋለንና ። በዛ ማግባት፣ መጋባት፣ ልጅ መውለድ የለም ። የሚወለደው ያለመሞት ብቻ ነው ። ያለው አንድ ነገር ፈጣሪን እያመሠገኑ መኖር ብቻ ነው ። በክርሥትና በእሥልምና ይሁን በአይሁድ ኃይማኖት ፤ ሰው ከሞተ በኋላ ሥጋው እንጂ ጠፊ ነፍሱ  እሥከ ዘላለም በገነት አልያም በሲዖል  ትኖራለች ። ይላሉ ።

በበኩሌ ሥለገነትና ሥለ ጋሃነም ሲወሳ ፈጣሪ ሥለማያሥፈራራ የየኃይማኖቱን … ማሥፈራርቾ አላምንበትም ። ፈጣሪ የበዛ ምህረትና ይቅርታ አለው ። በእኛ አእምሮም የሚመዘን አይደለም ። ሁላችንም ሸክላዎቹ ነን ። ነጩም ሆነ ጥቁሩ ፤ እናም በበዛ የነጭ ሚሲዮኖች ማሥፈራርቾ እግዛብሔርን እንደጨካኝ ዓምላክ መቁጠር ተገቢ አይደለምና ፈጣሪን የምናመልክ ከሆነ በቅን መንገድ ሁሌም በጥንቃቄ እንጓዝ ። በሞት ፣  ሥጋ    ወደአፈሩ እሥኪመለሥ  ፣ ለኑሯችን መጣፈጥ   የሚበጀን መልካም መሥራት ነውና ለመልካምና ለበጎ ነገር እንትጋ !  ሥለ ገነት ደግሞ ከሞት በኋላ እንደርስበታለን ። እሥከዘው ግን በበጎ ፈቃድ በመልካምነት ለመኖር እንጣር ።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Previous Story

“አሜሪካ የታጠቁ ሃይሎችን መደገፏን የኢትዮጵያን መንግስት ስም ማጥፋቷን ማቆም አለባት” ጋዜጠኛ ሄርሜላ አረጋዊ

Next Story

እስክንድር፣ ጃዋር፣ በቀለ ገርባና ስብሃት ነጋን ጨምሮ በእስር ላይ የነበሩ የፖለቲካ መሪዎች በምህረት ተፈቱ

Go toTop