¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
10 . መልአኩም እንዲህ አላቸው፦ እነሆ፥ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ፤
11 . ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና ።
12 . ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ ።
13 . ድንገትም ብዙ የሰማይ ሠራዊት ከመልአኩ ጋር ነበሩ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ ፦
14 . ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ ።
* እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ ።
ሰውን ከሞት ወጥመድ ለማዳን ና በጎ ፈቃድን ለማንገስ ነው ክርስቶስ ኢየሱስ ወደዚች ምድር የመጣው ። ይሁን እንጂ ዓምላክ እንደጠበቀው በዚች ምድር በጎ ፈቃድ አልነገሰም ። ዛሬም የዳቢሎስ ጥፋት በሰው የዕለት ፣ ዕለት ጭካኔ ይገለፃል ።
ከዩናይትድ እስቴት ኦፍ አሜሪካ እስከ አውሮፓ ፤ ከኢሲያ እስከ ላቲን አሜሪካ ፤ ከአፍሪካ ፣ ከገልፍ አገሮች እስከ አውሥትራሊያ ሰው በግለኝነት ና በስግብግብነት አጥር ውሥጥ ራሱን በማኖሩ በዓለም ላይ በተለይም በአፍሪካ ና ከሳህራ በታች ባሉ አገሮች የሰው ሥቃይ በዝቷል ።
ከነዚህ ከገራት ውጪ ፣ በሶሪያ ፣ በየመን ፣ በሱማሊያ ፣ በሱዳን እንሆ ዛሬ ና አሁን በካዛክስታን ሴጣን የሰውን አእምሮ ተቆጣጥሮ ይደንሳል ። እንዲህ ዓይነቱ አሥጠሊ ተግባር ሁሉ ከሰዎች መልካም ፈቃድ ማጣት የሚከሰት ነው ። ከዚ በታች ያሰፈርኩት በሉቃስ ወንጌል ላይ የተፃፈው ፣ የኢየሱስ ክርስቶስ የበጎ ፈቃደኝነት ተምህርት ሰው በምድር ላይ በሚቆይባት ጥቂት ቀን ቢተገብረው በሥጋ ና በነፍሱ የሚጠቅመው ነው ።
ሉቃስ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
25 እነሆም፥ አንድ ሕግ አዋቂ ሊፈትነው ተነሥቶ፦ መምህር ሆይ፥ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ? አለው ።
26 . እርሱም፦ በሕግ የተጻፈው ምንድር ነው? እንዴትስ ታነባለህ? አለው ።
27 . እርሱም መልሶ፦ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም አሳብህም ውደድ፥ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ አለው ።
28 . ኢየሱስም፦ እውነት መለስህ፤ ይህን አድርግ በሕይወትም ትኖራለህ አለው ።
29 . እርሱ ግን ራሱን ሊያጸድቅ ወድዶ ኢየሱስን፦ ባልንጀራዬስ ማን ነው? አለው ።
30 . ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለ፦ አንድ ሰው ከኢየሩሳሌም ወደ ኢያሪኮ ወረደ በወንበዴዎችም እጅ ወደቀ፤ እነርሱም ደግሞ ገፈፉት ደበደቡትም በሕይወትና በሞት መካከልም ትተውት ሄዱ ።
31 . ድንገትም አንድ ካህን በዚያ መንገድ ወረደ አይቶትም ገለል ብሎ አለፈ ።
32 . እንዲሁም ደግሞ አንድ ሌዋዊ ወደዚያ ስፍራ መጣና አይቶት ገለል ብሎ አለፈ ።
33 . አንድ ሳምራዊ ግን ሲሄድ ወደ እርሱ መጣ አይቶትም አዘነለት ፥
34 . ቀርቦም ዘይትና የወይን ጠጅ በቍስሎቹ ላይ አፍስሶ አሰራቸው፥ በራሱ አህያም ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማደርያ ወሰደው ጠበቀውም ።
35 . በማግሥቱም ሁለት ዲናር አውጥቶ ለባለቤቱ ሰጠና፦ ጠብቀው፥ ከዚህም በላይ የምትከስረውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ አለው ።
36 . እንግዲህ ከነዚህ ከሦስቱ በወንበዴዎች እጅ ለወደቀው ባልንጀራ የሆነው ማንኛው ይመስልሃል ?
37 . እርሱም፦ ምሕረት ያደረገለት አለ። ኢየሱስም፦ ሂድ አንተም እንዲሁ አድርግ አለው ።
ይሁን እንጂ ዓለም በዝንጋታ ገመድ ሥለምትጎትተን ሁላችንም የዛሬ ጥጋባችንን እንጂ የነገ ህመምን ፣ ሥቃይን ፣ የሞት ጣርን ወዘተ ። ድንገት እንደ ውሃ ሙላት እንደሚመጡብን ፈፅሞ አንገነዘብም ። እናም በዛሬው በታላቅ ምሥራች ና ከሞት ወጥመድ የመዳን ቀን ፣ በዝንጋታ ገመድ ዓለም እንደምትጎትታቸው ለማያሥተውሉ ፣ በተግባር ቃሉን ለማይፈፅሙ ፣ በቃል ግን ወንጌልን ለሚያነበንቡ ፣ ከጳጳሱ ብሰው በአንደበታቸው ጤፍ ለሚቆሉ ፣ እምነት ና ኃይማኖትን መሸቀጫ ላደረጉ ሥለ እውነተኛው እምነት ና ኃይማኖት በግል በተረዳሁት ልክ ልፅፍ ወደድኩ ።
ወድሞቼ ሆይ ! ሰዎችን ፣ ” ቀናና በጎ ሁኑ ! ” ከማለቴ አሥቀድሞ እኔ ራሴ ከአሥርቱ የፈጣሪ ትዕዛዛት ሥንቱን እንዳከበርኩ እጠይቃለሁ ።( … )እናም ሐጢያተኝነቴን አምኜ ያለአንዳች ፍርሐት ከመኃሪው ፈጣሪ ከኢየሱስ ክርስቶስ ) ፊት በፀፀት እቆማለሁ ። እናም ይምረኛል ። ሐጢያቴን ይቅር ይለኛል ። ያሥተሰርይልኛል ። የእኔ እምነት ሐጢያተኝነቴን ማመን ነው ። ፃድቅ አይደለሁም ። እምነቴ እንደ ፈቃዱ መኖር ነው ። ፈጣሪ በእኔ የሚተገብረው ፍቃድ አለው ። በእያንዳንዱ ፍጥረቱም የራሱ ፈቃድ አለው ።
አንተ ሰው ፣ ወደ ፈጣሪ ፊት ለመቅረብ ሁሉም ሰው መብት አለው ። ፀሎት ቻለ አልቻለ ። መሥፈርት የለውም ። ሰውኛ ነው መሥፈርቱ ። ፈጣሪ በቲኦሎጂ የፕሮፊሰር መዓረግ ሥላለህ ዘወትር አንተን አያዳምጥህም ። ወንድሜ ከእያንዳንዱ ፍጡር አእምሮ ጋር የፈጣሪ መንፈሥ የተገናኘ ነው ። የተቆራኘ ነው ።የተቆላለፈ ነው ። ልክ እንደ ሸማኔ ድር ። ደሞም ፈጣሪ ሰው አይደለም ። የትም የሚገኝ ሁሉን ቻይ መንፈሰ ነው እንጂ ። ለሰው ፊትም አያዳለም ና እኔንን ከሌላው ሰው አብልጦ አይወደኝም ። ኢየሱስ ፃድቃንን ፍለጋ አልመጣም ። ከፈሪሳውያንም ጋር አልበላም ና ጎስቋላውን እና ምሥኪኑን አላዛርን ከእኔ ይልቅ ይወደዋል ። ኢየሱስ ክርስቶስ የፈጣሪን አመለካከት ሊያሳየን ፈልጎ በምድር የ3 ዓመት ቆይታው ይኽንን አድርጓል ። …
የሰውን ብልጣ ብልጥነት ፣ ጅልነት ና የዘወትር የጠልፎ መጣል ሩጫውን ፣ የኑሮ ገመድ ጉተታውን፣ ክፋቱን ፣ ምቀኝነቱን ፣ ሥግብግብነቱን እዚህ ማንሳት አያሥፈልገኝም ። ደግሞም በተሰጠው መክሊት ተጠቅሞ ሥለበለፀገውና መክሊቱን ቀብሮ ለከሰረው ሰው ፣ ሰው ነኝ ና የምመክረው ምክር የለኝም ።… ደሞስ ፣ ለእያንዳንዱ ሰው ፈጣሪ የሰጠው እንጀራ ላይ እኔን ማን ወጥ ጨላፊ አደረገኝ ?!
በበኩሌ ፣ ወጥ መጨለፍ የምፈልገው በህይወት ላይ ነው ። ሰው ከጥበብ ወጥ እያጠቀሰ ይበላ ዘንድ እንሆ እጋብዘዋለሁ ።..
ሰዎች ሆይ ! ሁላቸውም ታውቃላችሁ ። በዓለም፣ የተለያዩ ኃይማኖቶች ና ኃይማኖተኞች እንዳሉ ። ብዙዎቹ በፈጣሪ መኖር የሚያምኑ እና ከሞት በኋላ ሁለተኛ የመኖር ዕድል አለ የሚሉ ናቸው ። ሁሉም ኃይማኖቶች ሐጢያትን ይከለክላሉ ። ሰዎች ግን ሐጥያትን በየቀኑ ይሰራሉ ። ላለመሥራት የሚጠነቀቁ ብዙ አማኞች አሉ ። ግን ግን ጥንቃቄ ሐጢያት ከመሥራት አይጠብቃቸውም ።በተግባር ባይሰሩም ፣ በአይንና በአንደበት ሐጢያትን ሳይገነዘቡት ይሰራሉ ። በአንደበታቸው ሐጢያትን በየቀኑ ሺ ጊዜ ይፈፅማሉ ። ( አንደበት ክፉ ብልት ነው ፣ ማንም ሰው አይቆጣጠረውም ። ይላል መፀሐፈ ቁልቁሉ ። )
ቤተ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ትንሳኤ ዘወትር በአንደበታቸው በመሥበክ ፣ ” ሰው ከሞት በኋላ በመንፈሥ ይነሳና የፈጣሪ አገልጋይ ሆኖ ለዘላለም ይኖራል ። ” በማለት ለፅድቅ እንድንተጋ ያሥጠነቅቁናል ። ሰው ከሞት በኋላ እየዘመረ ። እያመሠገነ ። በዘላለማዊ ሐሴት ውሥጥ ከፈጣሪ ጋር የመኖር ዕድል ፈንታ አለው እያሉ ተሥፋ ይመግቡናል ። ያለመሞትን በውሥጣችን እንድናረግዝ ያደርጉናል ። በገነት እንወልደዋለንና ። በዛ ማግባት፣ መጋባት፣ ልጅ መውለድ የለም ። የሚወለደው ያለመሞት ብቻ ነው ። ያለው አንድ ነገር ፈጣሪን እያመሠገኑ መኖር ብቻ ነው ። በክርሥትና በእሥልምና ይሁን በአይሁድ ኃይማኖት ፤ ሰው ከሞተ በኋላ ሥጋው እንጂ ጠፊ ነፍሱ እሥከ ዘላለም በገነት አልያም በሲዖል ትኖራለች ። ይላሉ ።
በበኩሌ ሥለገነትና ሥለ ጋሃነም ሲወሳ ፈጣሪ ሥለማያሥፈራራ የየኃይማኖቱን … ማሥፈራርቾ አላምንበትም ። ፈጣሪ የበዛ ምህረትና ይቅርታ አለው ። በእኛ አእምሮም የሚመዘን አይደለም ። ሁላችንም ሸክላዎቹ ነን ። ነጩም ሆነ ጥቁሩ ፤ እናም በበዛ የነጭ ሚሲዮኖች ማሥፈራርቾ እግዛብሔርን እንደጨካኝ ዓምላክ መቁጠር ተገቢ አይደለምና ፈጣሪን የምናመልክ ከሆነ በቅን መንገድ ሁሌም በጥንቃቄ እንጓዝ ። በሞት ፣ ሥጋ ወደአፈሩ እሥኪመለሥ ፣ ለኑሯችን መጣፈጥ የሚበጀን መልካም መሥራት ነውና ለመልካምና ለበጎ ነገር እንትጋ ! ሥለ ገነት ደግሞ ከሞት በኋላ እንደርስበታለን ። እሥከዘው ግን በበጎ ፈቃድ በመልካምነት ለመኖር እንጣር ።