በተቃውሞ እና ሁከት እየታመሰች ያለችው ድሬዳዋ ዛሬም አልተረጋጋችም፡፡ በተለይ መርመርሳ በተባለው ሰፈር ግጭቱ በቡድን በቡድን ሆነው በድንጋይ ሲወራወሩ እንደነበር የአይን እማኞች የገለጹ ሲሆም መከላከያና ፌዴራል ፖሊስ አካባቢውን ከበው ለማረጋገት መሞከራቸውን ነግረውናል::
https://www.youtube.com/watch?v=RvScL9Cy1vM&t=1064s
በከተማዋ የኢንተርኔት አገልግሎት ሲቋረጥ ስልክም በአግባቡ እየሰራ አለመሆኑን ለመረዳት ችለናል፡፡ ከጥቂት ቀናት በፊት የጥምቀት በአል አከባበርን ተከትሎ በከተማዋ የተጀመረዉ ግጭት ዛሬም ቀጥሎ ውሏል። በዛሬው ዕለት ባንኮች እና የንግድ ተቋማት ዝግ መሆናቸውን ከስፍራው የተሰራጩ ዘገባዎች ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም ድሬዳዋን ከሌሎች አካባቢዎች የሚያገናኙትም ይሁኑ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች በድንጋይ እንደተዘጉ ናቸው። ግጭቱ ዛሬ አምስተኛ ቀኑን የያዘ ሲሆን መንገድ መዝጋትና ንብረት ማዉደሙ ግን ሶስተኛ ቀኑን መያዙ ታውቋል፡፡
ተቃዋሚዎቹ ወጣቶች ‹‹የአስተዳደሩ ከንቲባ በአካል ቀርቦ ያነጋግረን፣ ለምናነሳቸዉ ጥያቄዎች መልስ ይስጠን›› የሚል ሃሳብ እንዳላቸው አበትላንትናው ዜናችን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ወጣቶቹ የጠየቁት ውይይቱ ባለመደረጉ ግጭቱ የተጀመረ ሲሆን ዛሬም ቢሆን የከተማዉ አስተዳደር ለወጣቶቹ ጥያቄ መልስ ባለመስጠቱ ‹‹አመራሩ ከስልጣን ላይ ይዉረድ›› የሚሉ መፈክሮች በከተማው እየጠሰሙ ነው፡፡ ምንጮች ተቃዋሚዎቹ ንብረቶችን የማዉደምና ወደ ሌላ ጥፋት እንዳይገቡ የመከላከያና የፌዴራል ፖሊስ አባላት ወጣቶች የማረጋጋት ስራ እየሰሩ እንደሚገኙ ገልፀዋል።
የከተማዉ ከንቲባ አቶ ኢብራሒም ኡስማን ‹‹የከተማዉን እዉቅና መንፈግ የሚፈልጉ ቡድኖች እና የቀድሞ የሶማሌ ክልል አስተዳደር ስር ተደራጅተው ይንቀሳቀሱ የነበሩ ወጣቶች ግጭቱ እንዲከሰት እና እንዲባባስ አድርገዋል›› ሲሉ ለሚዲያዎች ተናግረዋል። በዚህም የተጠረጠሩት ከ80 በላይ ሰዎች መታሰራቸዉን ከንቲባዉ ለአገር ዉስጥ መገናኛ ብዙሃን ገልፀዋል። ከንቲባው እስካሁን አንድ ሕጻን መሞቱን እና 10 ሰዎች ቀላል የመቁሰል አደጋ እንደደረሰባቸው ገልጸዋል።