አሁንገና ዓለማየሁ
የነጮች የበላይነት በነገሠባቸው ክፍለ ዘመናት ውስጥ አንድ አፍሪካውያንን የሚያኮራ ነገር የኦሮሞ “ዋቃ ጉራቻ” (ጥቁር እግዚአብሔር) የሚለው የአምላክን ቀለም አገላለጽ ነበር። ኦሮሞ አፍሪካዊና ጥቁር ሕዝብ ሆኖ አምላኩንም ጥቁር ነው ብሎ ማምለኩ አምላክ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጠረን የሚለው እና እኛ ጥቁር ከሆንን በአርአያውና በአምሳሉ ደግሞ ከፈጠረን የአምላካችንም ቀለም ጥቁር ነው ማለት ነው ወደ ሚል የተቃለለም ቢሆን አመክንዮአዊ (ሲምፕሊስቲክም ቢሆን ሎጂካል) መደምደሚያ የሚያደርሰውን ሃሳብ ያነገሠ ነበር። አምላክን በአምሳላቸው ፈረንጅ እያደረጉ እየሳሉ ያንንም ስእል በዓለም ላይ በመበተን በሌሎች ሕዝቦች ላይ የስነልቡና የበላይነት ለማሳደር ከመሞከርም ባለፈ ድፍረት ሰይጣንን ደግሞ በአፍሪካዊ ምስል አቅርበው የስነልቡና ስብራት ሲያካሂዱ ለኖሩት ምዕራባውያን “ዋቃ ጉራቻ” ወይም ጥቁር እግዚአብሔር ግሩም ሚዛን አስጠባቂ ነበር።
ታድያ ምን ያደርጋል ጥቂት የኦሮሞ ልጆች መንግሥታዊ ሥልጣንን በጠቀለሉበት ዘመን “ዋቃ ጉራቻ”ን በ”ዋቃ ዳለቻ” ለመተካት ሲጣደፉ ታዩ እንጂ።
መለኮታዊ ጉብኝት?
መቼም ድህነት የማያመጣው ጣጣ የለም። ሥጋን ያሸጣል፣ ነጻነትን ያሳጣል፣ ሃይማኖት ያስለውጣል። “ደሃ አታድርገኝ” ብሎ የጸለየው ማን ነበር? ወሃቢስቱ ዐቢይ አህመድ በጦርነት ድህነት ሲታሽ አንዱን ነጫጭባ መለኮት ብሎ በቅድስቲቱ ሀገር አምጥቶ በተዋህዶም በዋቄፈናም በእስልምናም ላይ ለማላገጥ መገደዱ የሚያሳፍር የታሪክ ቆሻሻ ነው።
ዐቢይ አህመድ ቢል ግራምን መለኮት ብሎ ያምጣው እንጂ አላማው ቢል ግራም የትራምፕ የነፍስ አባት ስለሆነ
“አማላጄ ድንግል አማላጄ” የሚለውን መዝሙር
“አማላጄ ቢል ግራም አማላጄ” ወደሚል ለመቀየር ነው የሚሉም አልጠፉም። የፋኖ ጦርነት ያስከተለበት የዶላር ድርቅ ያመጣበት ጦስ ነው በማለት።
እውነቱ እሱ ነው ወይስ ሐሰተኞች ነቢያት ይመጣሉ የሚለው ትንቢት የግድ ስለሆነ?
እንደዛም ከሆነ ዛሬ የተዋሕዶ አማኝ እንደ እባብ በደረሰበት በሚቀጠቀጥበት ዘመን
‘መለኮት’ ቢል ግራም በመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት የተነገረለት ሰው ሆኖ እናገኘዋለን ። እንዲህ ይነበባል።
ኢየሱስ በደብረ ዘይት ተራራ ተቀምጦ ሳለ ደቀ መዛሙርቱ ብቻቸውን ወደ እርሱ ቀርበው፣ “ይህ ሁሉ ነገር የሚሆነው መቼ ነው? የመምጫህና የዓለም መጨረሻስ ምልክቱ ምንድን ነው?” ሲሉ ጠየቁት። ኢየሱስም እንዲህ ሲል መለሰላቸው። ማንም ሰው እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ። ምክንያቱም ብዙዎች እኔ መሲህ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ። ብዙዎችንም ያስታሉ። የጦርነት ድምጽና የጦርነት ወሬንም ትሰማላችሁ። ይህ ሁሉ መሆን ስላለበት አትደንግጡ። በዚያን ጊዜ ሰዎች ለመከራ አሳልፈው ይሰጧችኋል። ይገድሏችኋል። በስሜም ምክንያት በሕዝቦች ሁሉ ዘንድ የተጣላችሁ ትሆናላችሁ። በዚያን ጊዜ ብዙዎች ሃይማኖታቸውን በመካድ ይሰናከላሉ። አንዱ ሌላውን አሳልፎ ይሰጣል፣ ሰዎችም እርስ በእርሳቸው ይጣላሉ፣ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያት ይነሳሉ፣ ብዙዎችንም ያስታሉ፣.. እነሱ ቢቻላቸውስ የእግዚአብሔርን ምርጦች እንኳን ለማሳሳት ታላላቅ ተአምራትና ድንቅ ነገሮችን ያሳያሉ።
ያም ሆነ ይህ ዓድዋ ባልተከበረበት የካቲት ወር፣ በዚያው በየካቲት በዓድዋ ድል የተመታው መንፈስ በምኒልክ ከተማ በአዲስ አበባ ሠልጥኖ የመታየቱ ጉዳይ ድሉ የተቀለበሰበትን መጠን አመላካች አድርገን ማየት ይገባናል።
ክርስቶስ መጥምቁ ዮሐንስን መንገድ ጠራጊ አድርጎ እንደመጣ “መለኮት” ቢል ግራምም ዐቢይ አህመድን በእሳትና በደም እያጠመቀ መንገድ እንዲጠርግለት አድርጎ መከሰቱን ልብ ይሏል። ጌታንና ሎሌን በአግባቡ መለየት ይበጃል ለማለት ነው።