መከላከያ ሰራዊት የደንብ ልብሱን ሊቀይር ነው

January 26, 2019

መከላከያ ሰራዊት የመለያ ደንብ ልብስ በመልበስ በሰራዊቱ ስም ወንጀል የሚፈፅሙ አካላትን ለመቆጣጠር የአባላቱን የመለያ ደንብ ልብስ የቀለምና የዲዛይን ለውጥ ሊያደርግ ነው፡፡

https://www.youtube.com/watch?v=p8iBU5RCUVc&t=50s

የመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ሜጀር ጀነራል አብዱራህማን እስማኤል ለመንግስት ሚዲያዎች ዛሬ እንደተናገሩት ደረጃውን የጠበቀ የደንብ ልብስ ለመለወጥ ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ ፋውንዴሽኑ በሚኒስትሮች ምክር ቤት በተሰጠው ስልጣን መሰረት ለሰራዊቱ አልባሳትና ሌሎች ወታደራዊ ግብዓቶችን አምርቶ ወይም ገዝቶ የሚያቀርብ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ የሚለወጠው የደንብ ልብስ የመከላከያ ሰራዊት አባላት የሚወዱት፣ በጥራት፣ በቀለምና በዲዛይን የተሻለ የመለያ ልብስ እንዲሆን ከተለያዩ አገሮች ተመክሮ መወሰዱን ገልጸዋል። የመከላከያ ጥናትና ምርምር ማዕከል ሃላፊ ብርጋዴር ጀኔራል ተሾመ ገመቹ በበኩላቸው የመከላከያ ሰራዊቱን አልባሳት መልበስ የሚችለው የሰራዊቱ አባል ብቻ መሆኑን ጠቁመው ይሁንና ተገቢ ቁጥጥር ባለመደረጉ የማይመለከታቸው ግለሰቦች ሲለብሱት መታየቱን ጠቁመዋል፡፡ አዳዲስ አልባሳት በሚቀርቡበት ወቅት አሮጌዎቹ በአግባቡ ሳይወገዱ በመቅረታቸው ልብሱ በማይመለከታቸው አካላት እጅ እየገባ የሰራዊቱን ስምና ክብር የሚያጎድፉ የተለያዩ ወንጀሎች እየተፈጸሙበት መሆኑን ገልጸዋል። የመከላከያ ሰራዊቱን የመለያ ደንብ ልብስ በመልበስ ወንጀል የሚፈጽሙ አካላት ካሉ በወንጀል እንደሚጠየቁ ተናግረዋል።

Previous Story

የጌታቸው አሰፋ ስውር እጆችና ብሔራዊ አደጋ | ከክንፉ አሰፋ

Next Story

የመንግስቱ ኃይለማርያም የቀኝ እጅ የነበሩት ሻምበል ለገሰ አስፋው ከዚህ አለም በሞት ተለዩ

Go toTop