ክፍል ፡ 10 የአማራ ህዝብ የህልወና አደጋ ምንጮች ብዙ ናቸው። ሁሉን አደጋዎች በአንድ ጊዜ መጋፈጥ አይቻልም።
• በአሁኑ ወቅት ለሁላችንም በቅድሚያ የሚታየን አደጋ አካላዊ የሆነው የህልውና አደጋ ነው። የአብይ አህመድ ጸረ አማራ ስትራተጂ የአማራን ህዝብ በማፈናቀል፣ በዘር ማጽዳት፣ ከድሮን እስከ ጀት በመጠቀም መጨፍጨፍ፣ በረሃብ እንዲረግፍ በጤና አገልግሎት አለመኖር እንዲያልቅ ማድረግ ነው። አብይ አህመድ ስልጣን ከያዘ ጀመሮ ይህን ስትራተጂውን በተግባር በማዋል በአማራ ህዝብ ላይ ከመቼውም ዘመን ታይቶ በማይታወቅ መጠን እንዲያልቅ አድርጓል።
• የህልወና ትግሉ አስቸኳይ ወይም የወዲሁ ግብ በአማራ ላይ አብይ አህመድ ያወጀውን በአካል የማጥፋት እኩይ ህልም ማምከን ነው። ሆኖም ግን የአማራ ህልውና በሚገባ እንዲጠበቅ፣ ህልውናው አስተማማኝ በሆነ መሰረት ላይ እንዲገነባ ከፈለግን አሁን የተከፈተበትን አካላዊ ጥቃት ከመመከት በላይ የተሻገሩ ችግሮችን ለመፍታት አልሞ የተነሳ መሆን ይገባዋል።
• የአማራ ህልውና አደጋ በኢኮኖሚ፣ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ፣ በትምህርት በጤና አገግሎት በምግብ ራስን ካለመቻል ጋር ይያዛል። ከመልካም አስተዳደር መጥፋት፣ የህዝብን ሃብት ከመዝርፈ ችግሮች ጋር ይተሳሰራል። እነዚህን ችግሮች አሁን ትግሉ ባላበት ደረጃ፣ ከሌሎች አንገብጋቢ ጥያቄዎች እኩል ቦታ ላይሰጣቸው ይችላል። በቅድሚያ አካላዊ ህልውናን ማስከበር ስለሚገባ። ሆኖም ግን የፋኖ ንቅናቄ መልክ ያለው፣ በሚገባ የተደራጀ የጋራ አመራር ሲኖረው፣ እነዚህ ጉዳዮች የህልውና ትግሉ አካል ሆነው መታየት የሚችሉበት ሁኔታ መፈጠር ይኖርበታል።
• አማራው የሚታገለው በማንነቱ ከሚያጠቁትና ከሚዘርፉት ጸረ አማራ ሃይሎች አካላት ለመላቀቅ ብቻ አይደለም። ተመሳሳይ ጥቃት ከሚያደርሱበት ከአብራኩ ከወጡ ግፈኞችና ዘራፊዎችም ነጻ ለመሆን ነው። ትግሉ ነጻነቱን እና መብቱን ሊገፉት ከሚችሉ ከየትኞቹም አካላት ጭምር ነጻ ለመሆን የሚደረግ መሆኑን ካሁኑ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል። በትግሉ ወቅት የሚገነቡ፣ የነጻነት፤ የፍትህ፣ የህዝብ ተቆርቋሪነት፣ የህዝብ መብት አክባሪነት፣ የህዝብ ሃብት ተነከባካቢነት ባህሪያት ከትግል በኋላ ለሚመሰረተው ፍትሃዊና ስብአዊ ማህበረሰብ እርሾ ሆነው ያገለግላሉ።
• ትግሉ አካላዊ ህልውናን ማስከበር ብቻ ሳይሆን፣ ሁለንተናዊ የአማራን ህዝብ ትንሳኤ በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፉ ለማምጣት እንደሆነ ካሁኑ ግንዛቤ ከያዝን፣ ሌሎች ማሳካት ያልቻሉትን፣ አንድን የከፋ ስርአት አስወግደን ካስወገድነው በከፋ ስርአት የሚተካበትን አሳዛኝ የታሪክ አዙሪት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መቅበር እንችላለን። መጪውን ካለፈው የተሻለ ለማድረግ ምን በማድረግ ነው የሚል ጥያቄ አንስተን ምላሹን መስጠት የትግሉ አካል መሆን ይገባዋል። ይህ ጥያቄ አሁን ይነሳ እያልኩ አይደለም። የፋኖ የጋራ አመራር እንደተቋቋመ ደረጃውን እና ጊዜውን ጠብቆ መነሳት ያለበት ጥያቄ መሆኑን ለማስገንዘብ የቀረበ ነው።