ግለሰቦች የገዙት ኮንደሚኒየም ቤት ውስጥ ገብተው አንወጣም በሚል ነዋሪዎችን እንዳባረሩ ትናንትና ከትናንት በስቲያ የተዘገበላቸው በሃረሪ ክልል የሚገኙ የተደራጁ ወጣቶች ዛሬ ደግሞ መንግስታዊውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ቢሮ ንብረትን ልቀቁ ማለታቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ለዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ተናግረዋል::
https://www.youtube.com/watch?v=J8BZqY2t65c
በሃረሪ የተደራጁ ወጣቶች የክልሉን የጸጥታ መዋቅር እያፈረሱ ነው የሚሉት ነዋሪዎቹ የሐረሪ ክልል ፖሊስ ኮምሽን ቅጥር ግቢን አቃጥለው ሙሉ በሙሉ የአድማ መበተኛ ንብረቶችን ማውደማቸውን ነግረውናል:: የሃረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ ግን እሳት ቃጠሎውን ማን እንዳስነሳው ሳይገልጽ “የተነሳውን የእሳት አደጋ ጉዳት ከማድረሱ በፊት በቁጥጥር ሰር አውዬዋለሁ” ብሏል::
የኮምሽኑ የህዝብ ግንኙነት ዲቪዝን ኃላፊ ኢንስፔክተር ረምዚ ሱልጣን እንደገለጹት አደጋው የተከሰተው በኮምሽኑ አባላት ማረፍያ ክፍል ውስጥ ነው:: አንድ ሰዓት ላይ በተነሳው የእሳት ቃጠሎ በሰው ህይወትና አካል ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰም:: ወደ ስምንት የሚጠጉ አባላቱ የሚያርፉባቸው ፍራሾችና የተወሰኑ የአድማ መበተኛ ቁሳቁሶች ተቃጥለዋል” ብለዋል::
“የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን የእሳት አደጋ መከላከል ክፍል ባደረገው ርብርብ አደጋው ወደ ሌላ ክፍል ሳይዛመት የከፋ ጉዳት ሳያደርስ መቆጣጠር መቻሉን የገለጹት ኃላፊው “የክልሉ ፖሊስ አባላት ላይ የሚታየው መከፋፈል ለአደጋው መንስዔ ሆናል ለሚለው” የአንዳንድ ወገኖች አስተያየት ኢንስፔክተር ረምዚ ሲመልሱ አደጋው ከዚህ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንደሌለው አስረድተዋል።
የሃረሪ ክልል ፖሊሶች መከፋፈላቸው በተለይ በከተማዋ ስርዓት አልበኝነት እንዲነግስና የተደራጁ ወጣቶች የፈለጉትን እንዲያደርጉ ምክንያት ሆኗቸዋል የሚሉት ለዘ-ሐበሻ አስተያየት የሰጡት ነዋሪዎች በከፍተኛ ስጋት ውስጥ መሆናቸውንና የዶ/ር አብይ የፌዴራል አስተዳደር መፍትሄ እንዲሰጣቸው ይጠይቃሉ::
የተደራጁት ወጣቶች መንግስታዊው የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ቢሮ በመሄድ ንብረቱ የኛ ነው በሚል እንዲለቁ ማስገደዳቸውን የነገሩን የድርጅቱ ሰራተኞች አዲስ አበባ ለሚገኘው ዋናው የኢዜአ ቢሮ ጉዳዩን ማሳወቃቸውንና የአዲስ አበባው ቢሮም ለመንግስት ጉዳዩን አሳውቆ ምላሽ እየጠበቀ መሆኑን እንደገለጸላቸው ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉት ወገኖች ነግረውናል::
–